Showing posts with label ከቤተ ደጀኔ. Show all posts
Showing posts with label ከቤተ ደጀኔ. Show all posts

Saturday, April 11, 2015

ትንሣኤ ዘክርስቶስ /የክርስቶስ ትንሳኤ/ መልአከ ሰላም ቀሲስ ደጀኔ ሺፈራው



በስመአብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን።

፩፥፩፤ ሦስት መዓልት እና ሦስት ሌሊት በመቃብር፦                  ፩፥፯፤ በኲረ ትንሣኤ፦
፩፥፪፤ ሦስት መዓልት እና ሦስት ሌሊት የሞላው እንዴት ነው?     ፩፥፰፤ ከትንሣኤው በኋላ ለምን ተመገበ?
፩፥፫፤ እንዴት ተነሣ?                                                   ፩፥፱፤ ለምን አትንኪኝ አላት?
፩፥፬፤ ለምን በአዲስ መቃብር ተቀበረ?                                ፩፥፲፤ ተስፋ ትንሣኤ፦
፩፥፭፤ እንዴት በዝግ መቃብር ተነሣ?                                  ፩፥፲፩፤ ሙታን እንዴት ይነሣሉ?
፩፥፮፤ መቃብሩን ማን ከፈተው?                                       ፩፥፲፪፤ የትንሣኤ ጸጋ፦

ጌታችን  አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ድኅነተ ዓለምን በመስቀል ላይ ከፈጸመ በኋላ በአካለ ሥጋ ወደ መቃብር ወረደ÷ ይኸውም በመቃብር ፈርሶ በስብሶ መቅረትን ሊያስቀርልን ነው፡፡ በአካለ ነፍስ ደግሞ ወደ ሲኦል ወረደ÷ ይኸውም በሲኦል ለነበሩ ነፍሳት ነፃነትን ይሰብክላቸው ዘንድ ነው፡፡ መለኮት፥ በተዋሕዶ፥ ከሥጋም ከነፍስም ጋር ነበረ፡፡ ለዚህ ነው፥ መቃብር ሥጋን ሊያስቀረው ያልቻለው፤ ሲኦልም ነፍስን ማስቀረት አልተቻለውም፡፡ ቅዱስ ዳዊት፡- « ነፍሴን በሲኦል አትተዋትምና ቅዱስህንም መበስበስን ያይ ዘንድ አትተዋትም» ያለው ይኽንን ታላቅ ምሥጢር በትንቢት ቃል ሲናገር ነው፡፡ መዝ ፲፭÷፲፡፡ ሐዋርያው  ቅዱስ ጴጥሮስም፡- «ክርስቶስ ደግሞ ወደ እግዚአብሔር (ወደ አብ÷ ወደ ራሱና ወደ መንፈስ ቅዱስ) እንዲያቀርበን፥ እርሱ ጻድቅ ሆኖ ስለ ዓመፀኞች አንድ ጊዜ በኃጢአት ምክንያት (ስለ ሰው ልጆች ኃጢአት ተላልፎ በመሰጠት) ሞቶአልና፤ በሥጋ ሞተ (በፈቃዱ ነፍሱን ከሥጋው ለየበመንፈስ ግን ሕያው ሆነ÷ (ያን ሥጋ ነፍስ እንድተለየችው መለኰት አልተለየውምበእርሱም ደግሞ (መለኰት በተዋሐዳት ነፍስ) ሄዶ በወኅኒ ለነበሩት ነፍሳት ሰበከላቸው፤» ብሏል።

፩፥፩፦ ሦስት መዓልት እና ሦስት ሌሊት በመቃብር
ጌታችን በከርሰ መቃብር የቆየው ሦስት መዓልትና ሦስት ሌሊት ነው፡፡ «ሥጋዬ ደግሞ በተስፋ ታድራለች፤» የሚለው ቃለ ትንቢት የሚያረጋግጥልን ይኽንኑ ነው፡፡ መዝ ፲፭፥፱፡፡ ምሥጢራዊ ትርጉሙም «ወደ መቃብር የወረደ ሥጋዬ በተስፋ ትንሣኤ ሦስት መዓልትና ሦስት ሌሊት በመቃብር አደረ፤» ማለት ነው፡፡ ተስፋ ትንሣኤውም በተዋሕዶ ከሥጋ ጋር ወደ መቃብር የወረደ መለኰት ነው፡፡ ነቢዩ ሆሴዕም፡- «÷ ወደ እግዚአብሔር እንመለስ፤ እርሱ ሰብሮናልና÷ (በሞተ ሥጋ ላይ ሞተ ነፍስን ጨምሮ የፈረደብን እርሱ ነውእርሱም ይፈውሰናል፤ (መርገመ ሥጋን መርገመ ነፍስን አስወግዶ ከሞት ወደ ሕይወት ያሸጋግረናል) እርሱ መትቶናል÷ እርሱም ይጠግነናል፡፡ ከሁለት ቀን በኋላ ያድነናል፤ በሦስተኛውም ቀን ያስነሣናል፡፡» በማለት ትንሣኤ ክርስቶስ በሦስተኛው ቀን መሆኑን አረጋግጧል፡፡ ሆሴ ÷፲፪፡፡ ይልቁንም ጌታችን ራሱ በመዋዕለ ሥጋዌው፡- ከሽማግሌዎችና ከካህናት አለቆች ከጻፎችም ብዙ መከራ ይቀበልና ይገደል ዘንድ፥ በሦስተኛውም ቀን ይነሣ ዘንድ እንዲገባው ለደቀመዛሙርቱ በግልጥ ነግሯቸዋል፡፡ ማቴ ፲፮÷፳፩፡፡ በገሊላም ሲመላለሱ፡- «ወልደ ዕጓለ እመሕያው ክርስቶስ በሰዎች እጅ አልፎ ይሰጥ ዘንድ አለው÷ ይገድሉትማል÷ በሦስተኛውም ቀን ይነሣል፤» ብሏቸዋል፡፡ ማቴ ፲፯÷፳፡፡ ጻፎችና ፈሪሳውያንም ምልክት በጠየቁት ጊዜ፡- «ክፉና አመንዝራ ትውልድ ምልክት ይሻል÷ ከነቢዩም ከዮናስ ምልክት በቀር ምልክት አይሰጠውም፡፡ ዮናስ በዓሣ አንበሪ ሆድ፥ ሦስት ቀንና ሦስት ሌሊት እንደነበረ÷ እንዲሁ የሰው ልጅ (ወልደ ዕጓለ እመሕያው ክርስቶስ) በምድር ልብ ሦስት ቀንና ሦስት ሌሊት ይኖራል፡፡» ብሏቸዋል፡፡ ማቴ ፲፪፥፴፰-፵።

ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ፦ የቤተክርስቲያን ትምህርት፤ (ክፍል ፬) መልአከ ሰላም ቀሲስ ደጀኔ ሺፈራው


          በስመአብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን።

                                                                      (ክፍል ፫ ለማንበብ እዚህ ይጫኑ)
 

ቅዳሴ ማርያምን በመንፈስ ቅዱስ ምሥጢር ገላጭነት የደረሰ አባ ሕርያቆስ ዘሀገረ ብህንሳ ነው። ሕርያቆስ ማለት፦ ለሹመት መርጠውታልና፥ ኅሩይ (ምርጥ) ማለት ነው። አንድም፦ ረቂቅ ምሥጢረ ሥላሴን ይናገራልና፥ ረቂቅ ማለት ነው። እርግጥ ከሊቃውንት ምሥጢረ ሥላሴን ያልተናገረ ባይኖርም፥ እርሱ አምልቶ አስፍቶ ተናግሯል። አንድም፦ አብ ፀሐይ፥ ወልድ ፀሐይ፥ መንፈስ ቅዱስ ፀሐይ ብሎ ጽፏልና ፀሐይ ማለት ነው። አንድም፦ የምዕመናንን ልቡና በትምህርቱ ብሩኅ ያደርጋልና፥ ብርሃን ማለት ነው። አንድም፦ ንብ የማይቀስመው አበባ እንደሌለ፥ እርሱም የማይጠቅሰው ሊቅ የለምና ንብ ማለት ነው።

ሹመትን በተመለከተ፥ ቅዱሳን ሐዋርያት፦ በትምህርቱ መናፍቃንን ተከራክሮ ይረታ ዘንድ የተማረ ይሾም፤ ይህም ባይሆን በጸሎቱ ስለሚጠብቅ፥ በትሩፋቱ ስለሚያጸድቅ፥ ባይማርም ግብረ ገብ የሆነ ሰው ይሾም ብለዋል። ይኸውም ትህትናው እስካለ ድረስ ውሎ አድሮ ተምሮ ምሥጢር ያደላድላል ብለው ነው። በዚህ መሠረት አባ ሕርያቆስ ትምህርት ባይኖረውም ግብረ ገብነት ነበረውና እልፍ መነኮሳትና እልፍ መነኮሳይት መርጠውታል። ግብረ ገብ በመሆኑም ሥርዓት ስላጸናባቸው መልሰው ጠልተውታል፥ ትምህርት ስላልነበረውም ንቀውታል። ከዕለታት በአንዳቸው ቀን በምን ምክንያት እንደሚሽሩት አስበው፥ «ቀድሰህ አቊርበን፤» አሉት። ትምህርት ስለሌለው አይሆንለትም ብለው በተንኰል ነው።

የአባ ሕርያቆስ ተምኔቱ (ምኞቱ) እንደ ቅዱስ ኤፍሬም፥ የእመቤቴ ምስጋና፦ እንደ ባሕር አሸዋ፥ እንደ ሰማይ ኮከብ በዝቶልኝ፥ እንደ ምግብ ተመግቤው፥ እንደ መጠጥ ጠጥቼው፥ እንደ ልብስ ለብሼው የሚል ነበር። የጠሉት እና የናቁት ሊቃውንት፥ «ከሊቃውንት ቅዳሴ የሚያስቸግረውን የቱን እናውጣለትእያሉ፥ በኅሊናቸው ሲያወጡ ሲያወርዱ፥ ሥርዓተ ቅዳሴውን ጨርሶ ከፍሬ ቅዳሴ ደረሰ። በዚህን ጊዜ፦ የለመኗትን የማትነሳ፥ የነገሯትን የማትረሳ እመቤት ገልጣለት «ጐሥዓ ልብየ ቃለ ሠናየ ከሚለው አንሥቶ፥ ወይእዜኒ ንሰብሖ ለአብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ፤» እስከሚለው ድረስ ሰተት አድሮጎ ተናግሮታል።

ብፁዕ አቡነ ቀውስጦስ፦ «ክፉ ሰው የሚለውን አያጣም፤» እንዳሉ፥ እነዚያ የሚጠሉትና የሚንቁት ሊቃውንት፦ «ይህ፦ የተናገሩትን ቀለም እንኳ አከናውኖ መናገር የማይቻለው፥ ዛሬስ እንግዳ ድርሰት እድርሳለሁ ብሎ አገኝ አጣውን ይቀባጥራል፤» ብለው አጣጣሉበት። የሚወዱት እና የሚያከብሩት ግን፦ «እንዲህ ያለ ምሥጢር ከመንፈስ ቅዱስ ነው እንጂ ከእሩቅ ብእሲ የሚገኝ አይደለም፤» ብለው አጸደቁለት። በዚያውም ላይ «ጽፈን ደጉሰን እንያዘው፤» አሉ። የጠሉት ግን ከንቀታቸው ብዛት «ማን ተናገረው ብለን እንይዘዋለንብለው ተቃወሙ። የሚወዱትና የሚያከብሩትም መልሰው «እንደ ልማዱ አድርገን አንይዘውምንአሉ። በሀገራቸው ልማድ እንግዳ ድርሰት የተደረሰ እንደሆነ፥ ጽፈው ደጉሰው ከእሳት ይጥሉታል፥ ከእሳት ደህና የወጣ እንደሆነ ከውኃ ይጥሉታል፥ ከውኃ ደህና የወጣ እንደሆነ ከሕሙም ላይ ይጥሉታል፥ ታማሚውን የፈወሰው እንደሆነ ደገኛ ድርሰት ነው ብለው ይይዙታል። የአባ ሕርያቆስንም ድርሰት ከእሳት ቢጥሉት በደህና ወጣ፥ ከውኃ ቢጥሉት በደኅና ወጣ፥ ከሕሙምም ላይ ቢጥሉት ፈወሰው፥ ይልቁንም ሙት አንሥቷል። በዚህን ጊዜ ደገኛ ድርሰት ነው ብለው አሥራ አራተኛ ቅዳሴ አድርገው ጠርዘውታል። አባ ሕርያቆስ በዚህ ድርሰቱ ያልተናገረው ምሥጢረ ሃይማኖት የለም። ምሥጢረ ሥላሴን፥ ምሥጢረ ሥጋዌን፥ ምሥጢረ ጥምቀትን፥ ምስጢረ ቊርባንን፥ ምሥጢረ ትንሣኤ ሙታንን አምልቶ አስፍቶ ተናግሯል።