Saturday, February 15, 2014

“ግብረ ሰዶማዊነት ሊለወጥ የሚችል ክስተት ነው!”


“ግብረ-ሰዶማዊያን” ማለት፥ ስድብ ሳይሆን የሚፈፅሙት ከመደበኛው የመሳሳብና አንድ የመሆንን በመግፋትና  በመናድ፤ የተመሳሳይ የፆታ ውሕደት ለመፍጠር የሚደረጉ ማንኛቸውም ግንኙነቶች  ልዩ መጠርያ ስማቸው “ግብረ-ሰዶማዊያን፤ የሰዶም ነፍሳት” ናቸው የሚባለውም ከዚህ ነባራዊ ሁናቴ ስለለወጡት ነው። ይህምግብረ-ሰዶማዊያንየሚለው መጠርያ ስማቸውም የተገኘው በሁለቱ ከተሞች ስም ነው። በእነዛ ከተማ የተደረገውን የተመሳሳይ የፆታ ፍትወት መሰረት በማድረግ፤ ከዚያን ጀምሮ  ስማቸው በእነዚ ከተማ ስም መጠራት ተጀመረ። (በነገራችን ላይ ሌዝቢያን አልያም ጌይ ካልተባልን የሚሉ ከሆነ ደግሞሌዝቢያንማለትም የከተማ ስም እንደሆነ እናያለን።)
ከክርስቶስ ልደት በፊት 5 ክፍለ ዘመን ሌስቦስ በምትባል የግሪክ ደሴት እንስት የግጥም ጸሐፊ የሆነች ሳፕፎ በርካታ ወጣት ልጃገረዶችን ታስተምር ስለ ነበር ሌዝቦስ የሚለው የከተማው መጠሪያ ለእንስት ግብረ ሰዶማዊነት መጠሪያነት ውሏል፡፡ የእንግሊዘኛው ልዝቢያን የሚለው ቃል የተወረሰው ከዚሁ የግሪክ ቃል ነው፡፡ሲል የግብረ-ሰዶማዊያኑ ድርጅት በድረ ገፃቸው ላይ አስፍረውታል። ቢሆንም ግን እኛ የስራቸውን የወረደ ቅለትና በመጀመሪያውኑ ላልተገባ ባህርያት እራሳቸውን ለሚያረክሱ ሰዎችግብረ-ሰዶማዊ ወይም ግብረ-ሰዶማዊትእንላለን ማለት ነው።
ግብረ-ሰዶማዊ ተፈጥሮ ነው ወይስ ተጋቦሽ? ለሚለው ጥያቄ፥ ግብረ-ስዶምማዊ ተፈጥሮ የለም። የአሜሪካው የስነ ልቦና ድርጅት (..) .. 1973 ባወጣው መግለጫ ግብረ-ሰዶማዊነት መደበኛ የሰው ተፈጥሮ ነው ብሎ ድንገት ማስታወቁ ትዝ ሊለን ይገባል፡፡ ከዚሁ ጋር ተያይዞ የስነ-ልቦናውና የአእምሮ ህክምና ጥናት ዘርፉ በግብረ-ሰዶማውያን ልዩ አጅንዳ የተጥለቀለቀ ይመስላል፡፡ ስለሆነም የቅርብ ጊዜ የግብረ-ሰዶማዊነት ላይ ጥናቶችም ( በተለይም ጸሃፊዎቹ ራሳቸው ግብረ-ሰዶማውያን ከሆኑ) በጣሙን ሚዛናዊነት የጎደላቸው፤ በዘርፉ በሚደረገው ጥናት ላይ የተመራማሪዎችን እውቀት ታማኝነት የማይገልጡ መሆናቸው ልናጤነው ይገባዋል፡፡
ይህም ማለት ሠዎች በመለማመድ ወይንም በተለያየ ምክንያት ወደዚህ ወደ ተገቢ ያልሆነ፣ የነውርና የኃጢአት ርኩሰት በሆነ፤ በተመሳሳይ ፆታ የሕይወት ውጣ-ውረድ ውስጥ ሲገቡ ሱስ ሆኖ ይፀናወታቸውና በዛው እራሳቸውን ለዚህ ግብረ ሰዶማዊነት እንደተፈጠሩ ያስባሉ። ይህ ሐሳባቸው፥ ደግሞ ለሕይወት ሥኬትቸው መቃናት የሚመኙላቸውን ሠዎችን፤ ግሳጼና ምክር አይሰሙም። 

መጽሐፍ ቅዱስን ማስተማር የሚገባቸው እነማን ናቸው? በመልአከ ሰላም ቀሲስ ደጀኔ ሽፈራው


(በዚህ በመልአከ ሰላም ቀሲስ ደጀኔ ሽፈራው፤ መንፈሳዊ ትምህር ላይ፥ እጅግ ጥልቅ ምጡቅና ምዕሉ፤ በሆነ ትምርታቸው፦ መጽሐፍ ቅዱስን እነማን ማስተማር እንደሚገባቸው፣ በተለ ፷፮ቱን መጽሐፍ ቅዱስ ብቻ ብለው ለተቀበሉት ዋና ዋና የመጽሐፍ ቅዱስን ፍሬ-ነገሮችን በጥያቄ ልክ በማንሳትና ለጥያ ነጥቦች መጽሐፍ ቅዱሳዊ ምላሾች በመስጠትና እናት ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ /ክርስቲያን በመንፈሳዊ አስተምህሮ እንዳላትና  አሰበጣጥራ በማዋሃድ በመተንተን እንደምታስተምረ፤ አስረግጠው ይናገራሉ! የአንደበታቸውን ቃል፣ የትምርታቸውን ማዕደ በረከ አብረን እንድንቋደስ፤ እነሆ፦ ከአባታችን ቃለ-ወንጌል የተወሰደ።)

            ጉዳያችን፥ ከምዕራፍና ከቁጥር ጋር ከሆነ

ለምሳሌ፦ እመቤታችንን ቅድስት ድንግል ማርያምን የተቀበልናት፤ በማን ስም ነው? በኢየሱስ ክርስቶስ ስም አይደል እንዴ! የክርስቶስ እናት ስለሆነች! ቅዱሳኑን የተቀበልነው በማን ስም ነው? በኢየሱስ ክርስቶስ ስም እኮ ነው! ነቢያትን፥ የተቀበነው በማን ስም ነው? በኢየሱስ ክርስቶስ ስም እኮ ነው! ሐዋርያትን፥ በኢየሱስ ክርስቶስ ስም! ጻድቃንን፥ በኢየሱስ ክርስቶስ ስም! ሰማዕታትን፥ በኢየሱስ ክርስቶስ ስም! መስቀሉን፥ በኢየሱስ ክርስቶስ ስም! ቁርባኑን፥ በኢየሱስ ክርስቶስ ስም! እንዴት! ማስተዋል አቃተን?

ጉዳያችን፥ ከምዕራፍና ከቁጥር ጋር ከሆነ፤ ነጥብ በነጥብ እንነጋገራለን! የማቴዎስ ወንጌል ምዕራፍ ቁጥር ፳፫፤ ቅዱስ ማቴዎስ ወንጌላዊ፥ ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ እንዲህ ብሎ ፅፏል፦ "በነቢያት፥ ናዝራዊ ይባላል የተባለው ይፈጸም ዘንድ፥ ናዝሬት ወደምትባል ከተማ መጥቶ ኖረ።" ማን? ኢየሱስ ክርስቶስ! የት ኖረ? በናዝሬት ኖረ! ለምን በናዝሬት ኖረ? "በነቢያት፥ ናዝራዊ ይባላል" ተብሎ የተነገረው ይፈጸም ዘንድ።

አሁን ይሄንን ትንቢት ይዘን የነቢያትን መጽሐት ብንመለከት፣ የነቢያትን መጽሐት ብንመረምር፤ ይሄንን ትንቢት አናገኘውም። ትንቢተ ኢሳያስ ላይ የለም "ናዝራዊ ይባላል" የሚለው ትንቢት። ትንቢተ ኤርምያስ ላይ የለም፣ ትንቢተ ሕዝቅኤል ላይ የለም፣ ትንቢተ ዳንኤል ላይ የለም፤ የነቢያት ትንቢት መጽሐት ሁሉ ላይ የለም። ታዲያ፥ ቅዱስ ማቴዎስ፥ ከየት አምጥቶ ጻፈው? ከየት አምጥቶ ነው "በነቢያት፥ ናዝራዊ ይባላል" ተብሎ የተነገረው ትንቢት ይፈጸም ዘንድ ይሆን፤ ያለው? ምዕራፍና ቁጥር ስጡኝ? ቶሎ በሏ! ቅዱስ ማቴዎስ ከየት አመጣው? በነቢያት መጽሐት ከሌለ ከየት አመጣ?

Sunday, February 9, 2014

ትምህርተ ጋብቻ ክፍል፦ ፫ በመልአከ ሰላም ቀሲስ ደጀኔ ሺፈራው

            ፩፦ መጠናናት፤
         ምንም እንኳን የሰው ልጅ ተጠንቶ የማያልቅ ሳይንስ ቢሆንም ፦ ወደ ትዳር ዓለም ከመግባት በፊት ፦እንደ ሰው፥ በሰው አቅም መጠናናት እንደሚያስፈልግ ለማንም ግልጥ ነው። ይኸውም በሰከነ ልቡና ፥ በተረጋጋ መንፈስ ሊሆን ይገባል። በትውውቅ ሰሞን የተሸፈነ ብዙ ነገር ፥ በሂደት ቀስ እያለ ብቅ ማለቱ ስለማይቀር ጊዜ መስጠት ያስፈልጋል። ሰውን የምናጠናው ድካም የሌለበት ፍጹም የሆነ ሰው ለማግኘት አይደለም። ምክንያቱም እኛም ፍጹም አይደለንምና ነው ፥ አንድም በዓለመ ሥጋ ፍጹም ሰው አይገኝምና ነው። በመሆኑም፦ በእኛ ዘንድ ድካም እንዳለ ሁሉ ፦ በሌላም በኲል ድካም ሊኖር እንደሚችል አምነን ኅሊናችንን ልናዘጋጀው ይገባል። ከዚ ህ በኋላ ድካሙን ፦ በአራት ደረጃ ከፍለን ልናየው እንችላለን። ፩ኛ፦ በቶሎ የሚወገድ ድካም ፤ ፪ኛ ፦ በሂደት የሚወገድ ድካም፤ ፫ኛ፦ ልንሸከመው የሚገባን ድካም፤ ፬ኛ ፦ የማይወገድ ድካም፤

፩፥፩፦ በቶሎ የሚወገድ ድካም፤
         የሰው ልጅ በትምህርት ፥ በምክርና በተግሣጽ ፦ ከጥፋቱ ሊመለስ ፥ ከድካሙም ሊበረታ ይችላል። ስለሆነም ያሉትን ደካማ ጐኖች ዘርዝሮ በማውጣት ፦ እርስ በርስ መነጋገር ፥ መማማር ያስፈልጋል። ከአቅም በላይ የሆነውን ደግሞ ወደ ካህኑ በማምጣት ማስ መከር ይገባል። እንዲህ ዓይነቱ ድካም ፦ ከእውቀት ማነስ፥ ከመካሪ ማጣት ፥ አርአያ የሚሆን ሰው ካለማግኘት በመሆኑ በቶሎ ይወ ገዳል። ጠቢቡ ሰሎሞን፦ «ምክር በሰው ልቡና እንደ ጥልቅ ውኃ ነው፤ አእምሮ ያለው ሰው ግን ይቀዳዋል።» እንዳለ፦ አእምሮ ያላቸው የሚያስተውሉ ሰዎች ይስተካከሉበታል። ምሳ ፳፥፭። «ተግሣጽን የሚወድድ ዕውቀትን ይወድዳል፤» እንዲል፦ በሁሉ ይገሠጻሉ። ምሳ ፲፪፥፩። «የተማረ ልጅ ብልህ ይሆናል፤» እንዲል፦ ልባሞች ፥ አስተዋዮች እየሆኑ ይሄዳሉ። ምሳ ፲፥፭። ይህም ከምድራዊ ሀብት የሚበልጥ ሀብት ነው። ምክንያቱም « ከብር ይልቅ ትምህርትን ፥ ከተፈተነ ወርቅም ይልቅ ዕውቀትን ተቀበሉ ፤ » ይላልና። ምሳ ፰፥፲። «ትምህርትና ተግሣጽም የሕይወት መንገድ ነውና፤» የሚልም አለ። ምሳ ፮፥፳፫።

፩፥፪፦ በሂደት የሚወገድ ድካም፤
         በሰው ልጅ ሕይወት ፦ በአንድ ጀንበር ወይም በአጭር ጊዜ የማይወገድ የሥጋ ድካም አለ። አብሮ የኖረ ጠባይ እጅግ አስ ቸጋሪ ስለሆነ፦ በሂደት የሚወገድበትን መንገድ በመፈለግ በትዕግስት መጓዝን ይጠይቃል። የየዕለቱን ለውጥም መከታተል ያስፈልጋል። ዋናው ነገር ችግሩን አምኖ መቀበል ነው። እኛም በምክርና በትምህርት ድካማችንን ለማስወገድ ፥ ሕይወታችንን ለመለወጥ የሚታ ገሉትን ልናግዛቸው ያስፈልጋል። ይህ ጉዳይ ጾምና ጸሎትንም ይጠይቃል። መካሪው ክፍል «ፈጣሪ ሆይ ይህን ሰው እርዳው፤ » እያለ ፥ ድካም ያለበትም ሰው፦ « ፈጣሪዬ ሆይ፥ እርዳኝ፤ » እያለ ፦ ሊጾሙ ሊጸልዩ ይገባል። ጌታ በወንጌል፦ እንደተናገረ፦ ካልጾሙና ካልጸ ለዩ በስተቀር የማይለቅ ክፉ መንፈስ ፥ ክፉ ጠባይ አለና። ማቴ ፲፯፥፳፩።

         ጌታችን አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ፦ ወደ ቤተ ሳይዳ በደረሰ ጊዜ፦ አንድ ማየት የተሳነው ሰው ወደ እርሱ አመጡ ፥ እንዲዳስሰውም ለመኑት። ጌታም ያን ሰው እጁን ይዞ ከመንደር ካወጣው በኋላ፦ በዓይኑ ላይ እንትፍ ብሎ ዳሰሰውና፦ «ምን ታያለህ?» አለው። ያም ሰው በአንድ ጊዜ መዳሰስ አጥርቶ ማየት ባለመቻሉ፦ «ሰዎችን እንደ ዛፎች ወዲያና ወዲህ ሲመላለሱ አያለሁ፤» አለ። ጌታም ዳግመኛ ዳሰሰውና አጥርቶ እንዲያይ ፥ ፈጽሞም እንዲድን አደረገው። ዓይኖቹ ብሩህ ሆነውለት ሁሉንም ለመመልከት ችሏል። ልክ እንደዚህ በዕደ ምክር ደግሞ ደጋግሞ መዳሰስ የሚገባው ሕይወት አለ። በሂደትም እየጠራ ፥ እየተስተካከለ ይሄዳል።

ትምህርተ ጋብቻ ክፍል፦ ፪ በመልአከ ሰላም ቀሲስ ደጀኔ ሺፈራው

              ፩፡- የትዳር ጓደኛን ማን ይምረጥልን?
         የትዳር ጓደኛ በሰው ልጅ ሕይወት ውስጥ መሠረታዊ ጉዳይ ነው። ባለጸጋ ፥ወይም ባለሥልጣን፥ ወይም ቆንጆ፥ ወይም ጤነኛ፥ ስለሆኑ ብቻ የሚሹት አይደለም። ደሀ፥ ወይም ተርታ ሰው፥ ወይም መልከ ጥፉ፥ ወይም በሽተኛ ፥ቢሆኑም የሚፈለግ የሚናፈቅ ነው። ሳያገቡ ለመኖር የወሰኑትም ቢሆኑ ፥ፍላጎቱ ያለው በአፍአ ሳይሆን በውስጥ ስለሆነ፥ ከኅሊና ውጣ ውረድ ሊድኑ አይችሉም። ስለሆነም ከኅሊናቸውና ከፍላጎታቸው ጋር እየታገሉ በገድል ይኖራሉ። በዚህ ትግል ማሸነፍም መሸነፍም ሊኖር ይችላል። የትዳር ጓደኛ ከውጭ ወደ ውስጥ የምናስገባው ሳይሆን፥ ከውስጣችን ፈልገን የምናገኘው ነው። ይህም ማለት፡- በአዳምና ሔዋን ሕይወት እንዳየነው፡- እግዚአብሔር የትዳር ጓደኞቻችንን አስቀድሞ በእያንዳንዳችን ሕይወት ውስጥ አስቀምጧቸዋል። በመሆኑም አንድ ሰው ሥዕል (ፎቶ ግራፍ) ይዞ የሥዕሉን ባለቤት እንደሚፈልግ በውስጣችን የተቀመጠውን፥ የተሣለውን ይዘን መፈለግ ይገባል።

የሰው ልጅ በእምነቱም ሆነ በሌላው ነገር ሁሉ ፍጹምነት ስለሌለው በፍለጋው (በመንገዱ) አጋዥ ያስፈልገዋል። ያንንም የሚሰጠን ያለ ጥርጥር እግዚአብሔር ነው። ለዚሀም የጾምና የጸሎት ሰው መሆን ያስፈልጋል። የነቢያት አለቃ ሙሴ ጽላቱን ከእግዚአብሰሔር እጅ የተቀበለው አርባ መዓልትና አርባ ሌሊት ጾሞ ነው፥ እንጀራ አልበላም፥ ውኃም አልጠጣም። ዘጸ ፴፩፥፲፰። እኛም እንደ ጽላት እንደ ታቦት ተከብረው የሚያስከብሩ የትዳር ጓደኞቻችንን በጾምና በጸሎት ልናገኛቸው እንችላለን ብለን ልናምን ይገባል። በአገራችን፡-«አቶ እገሌ እኮ ታቦት ማለት ናቸው፥ ወ/ሮ እገሊት እኮ ታቦት ማለት ናቸው፤» የሚባሉ ነበሩ። ታቦት የሚያሰኛቸው የጸና ሃይማኖታቸው፥ የቀና ምግባራቸው ነበረ። ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ፡- «ኢተአምሩኑ ከመ ታቦቱ ለእግዚአብሔር አንትሙ፥ ወመንፈሰ እግዚአብሔር ላዕሌክሙ። እናንተስ የእግዚአብሔር ታቦት (ማደሪያ) እንደሆናችሁ፥ መንፈስ ቅዱስም አድሮባችሁ እንዳለ፥ እንደሚኖርም አታውቁምን? (አታስተውሉምን፥ ልብ አትሉምን)?» ያለው ለዚህ ነው። ፩ኛቆሮ ፫፥፲፮። የነቢያት አለቃ ሙሴ ጽላቱን ለመቀበል እስከ ደብረ ሲና ተጉዟል፥ አቀበቱን (ተራራውን) ወጥቷል። እግዚአብሔር የሚያሳየውን ሁሉ በትእግሥት ተመልክቷል፥ የሚነግረውንም ሁሉ በትእግሥት አድምጧል፥ የሰጠውንም በጸጋ ተቀብሏል። እኛም የምንሻውን ለማግኘት እስከ ቤተክርስቲያን በእግረ ሥጋ ብቻ ሳይሆን በእግረ ልቡና ጭምር መጓዝ አለብን። (ንስሐ መግባት፥ ሥጋ ወደሙ መቀበል፥ ዘወትር ማስቀደስ፥ ቃለ እግዚአብሔርን ማድመጥ ይጠበቅብናል)። ይኸንን ሁሉ ለማድረግ አቀበት ቢሆንብንም ከራሳችን ጋር ታግለን ማሸነፍ፥ ለነገሮች ሁሉ ትእግሥተኛ መሆን ይኖርብናል።

፩፥፩፡- የትዳር ጓደኛችንን ራሳችን መምረጥ አለብን፤
ልካችንን የምናውቀው ከማንም በላይ ራሳችን ነን። ራሳችንን ካልዋሸነው በስተቀር ለዓይናችን የሚሞላውን፥ የልባችንን ሚዛን የሚደፋውን፥ በልካችን የተሰፋውን ልብስ እናውቀዋለን። በመሆኑም ጊዜው ሲደርስ በጣም ሳንቸኩል፥ እጅግም ሳንዘገይ፥ እግዚአብሔር እንዳመለከተን ልንመርጥ ይገባል። ምክንያቱም መቸኰልም፥ መዘግየትም በየራሳቸው ችግር አለባቸውና ነው። ቸኩለውም ዘግይተወም የሚቸገሩና የሚጨነቁ፥ የሚበሳጩና የሚያማርሩ፥ ተስፋ ቆርጠውም እግዚአብሔር ትቶኛል፥ ረስቶኛል፥ የሚሉ ብዙ ሰዎች አሉ። በአገራችን፡- «የቸኰለ አፍሶ ለቀመ፥ የጅብ ችኩል ቀንድ ይነክሳል፥ የነቶሎ ቶሎ ቤት ዳርዳሩ ሰንበሌጥ፤» የሚሉ ሥነ ቃላት አሉ። መጽሐፍ ቅዱስ፡- እንኳን ለግብር ለነቢብ (ለመናገር) እንኳ መቸኰል እንደማይገባ ይመሰክራል። «ስለዚህ የተወደዳችሁ ወንድሞቼ ሆይ፥ ሰው ሁሉ ለመስማት የፈጠነ፥ ለመናገርም የዘገየ (ረጋ-ያለ)፥ ለቁጣም የዘገየ ይሁን፤»ብሏል። ያዕ ፩፥፲፱። ይኸንን በተመለከተ፡- «የረጋ ወተት ቅቤ ይወጣዋል፤» የሚል ሥነ ቃል አለ። እንዲህም ሲባል በጣም መዘግየት ይገባል ማለት አይደለም። ምክንያቱም፦  ለበጎ ነገር ሲሆን ሰይጣን ሰውን ሆን ብሎ የሚያዘገይበት ጊዜ አለና። ጌታችን አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ፡- የኤማሁስን መንገደኞች፡- «እናንት የማታስተውሉ፥ነቢያትም የተናገሩትን ሁሉ ልባችሁ ከማመን የዘገየ፤» በማለት ወቅሷቸዋል። መውቀስ ብቻ ሳይሆን ስለ እርሱ የተጻፈውን፡- ከሙሴ ኦሪትና ከነቢያት ትንቢት እየጠቀሰ ተርጉሞላቸዋል። ሉቃ ፳፬፥፳፭። ታላቁ ሐዋርያ ቅዱስ ጳውሎስ፡- «ሰይጣን አዘገየኝ፤» ያለበት ጊዜ አለ።

         እንግዲህ በጣም ሳንቸኵል፥ በጣምም ሳንዘገይ፡- የትዳር ጓደኛችንን እንምረጥ ስንል፡- «ስለ እኔ ማንም አያገባውም፤» በሚል መንፈስ፥ በራችንን ጥርቅም አድርገን ዘግተን አይደለም። የተዘጋ ቤት ንጹሕ አየር እንደልብ ስለማይገባው ይታፈናል። በዚህን ጊዜ ለመተንፈስ ያስቸግራል፥ ለአስምና ለተመሳሳይ በሽታዎችም ስለሚያጋልጥ ጤና ይታወካል። ለብቻው አእምሮውን ዘግቶ የሚያስብም ሰው እንዲሁ ነው። ስለዚህ አሳባችንን የምናጋራው፥ ጭንቀታችንን የምናካፍለው ሰው ያስፈልገናል። ቅዱስ ዳዊት፡- «ቀዳሚሃ ለጥበብ ፈሪሃ እግዚአብሔር፥ ምክር ሠናይት ለኵሉ ዘይገብራ። የጥበብ መጀመሪያ እግዚአብሔርን መፍራት ነው፥ ለሚያደርጋት ሁሉ ምክር መልካም ናት።» ያለው ለዚህ ነውና። መዝ ፻፲፥፲።

ትምህርተ ጋብቻ ክፍል፦ ፩ በመልአከ ሰላም ቀሲስ ደጀኔ ሺፈራው

                                   ፩፦ « መጋባት በሁሉ ዘንድ ክቡር ነው፤» ዕብ ፲፫፥፬
         ጋብቻን ባርኮና ቀድሶ ለሰው ልጅ የሰጠው እግዚአብሔር ነው። በመሆኑም ጋብቻ የእግዚአብሔር ጸጋ ነው። ስለዚህ በዓይን ምኞት ተጋርደው፥ በሥጋ ፍላጐት ተነድተው ፥ በስሜት ፈረስ ጋልበው ፥ የሚገቡበት ሳይሆን ፦ በጸሎት እና በምልጃ ፈቃደ እግዚአብሔርን ጠይቀው የሚፈጽሙት ታላቅ ምሥጢር ነው።
         ጋብቻ የሰው ሁሉ ሕልም ነው። የማይመኘው፥የማይፈልገው የለም። የሰው  ሁሉ ጸሎት፥ የሰው ሁሉ ስእለት ነው። ለመሆኑ፦ ህልሙ የተፈታለት ፥ ጸሎቱ የደረሰለት ፥ ስዕለቱ የሰመረለት ስንቱ ይሆን? ያላገባው ይናፍቃል ፥ ያገባው ደግሞ ያማርራል። ከጋብቻ በፊት « መልአክ » የተባለ የትዳር ጓደኛ ከጋብቻ በኋላ «ሰይጣን» ይባላል። «እኔ የመረጥኩትን ካላገባሁ እሰቀላለሁ፤» እንዳልተባለ «ካልተፋታሁ መርዝ እጠጣለሁ፤» ለማለት ችግር የለም። ከጋብቻ በፊት ምክር ላለመስማት አሳብ ላለመቀበል፦ «ስለ እኔ ማንም አያገባውም፤» ተብሎ በር እንዳልተዘጋ ሁሉ ከጋብቻ በኋላ ግን ጣልቃ የማያስገቡት ሰው  የለም ፤ «ምን በወጣህ ፥ ምን በወጣሽ፤» የሚለውን ፈጥኖ ለመቀበል በሩ ለሁሉም ክፍት ነው።
                                     ፪፦ ጋብቻ እንዴት ተጀመረ?
         ጋብቻ በአዳምና በሔዋን እንደተጀመረ የጎላ፥ የተረዳ ፥ የታወቀ ነገር ነው። «ተባዕተ ወአንስተ ገብሮሙ፤ ወንድና ሴት አድርጎ ፈጠራቸው፤ » እንዲል፦ አዳም ሲፈጠር ሔዋን በውስጡ ነበረች። ዘፍ ፩፥፳፰። ይህም በባህርዩ ነበረች ማለት ነው። አንድ አካል፥ አንድ ሥጋ ከሚያሰኛቸው ምሥጢር አንዱና ዋነኛውም ይኸው ነው።

         ጋብቻ የተጀመረው በአዳም ጥያቄ ነው፤ ጥያቄዎም የኅሊና ማለትም ውሳጣዊ ነበር። ምክንያቱም፦ ከላይ እንደተ መለከትነው፦ የትዳር ጓደኛው በውስጡ ስለነበረች ነው። « እግዚአብሔር አምላክም፦ ሰው ብቻውን ይሆን ዘንድ መልካም አይደለም፤ የሚመቸውን ረዳት እንፍጠርለት፥አለ፤»ይላል። እግዚአብሔር እንዲህ ማለቱ፦ በአዳም ኅሊና ውስጥ ይህ ጥያቄ እንደሚነሣ ስለሚያውቅ ነው። መናገሩም ለአዳም ኅሊና እንጂ ፥ ሔዋን ለአዳም እንደምትፈጠርለት አስቀድሞ በእግዚአብ ሔር ዘንድ የተወሰነ ነው።
         እግዚአብሔር፦ የምድር አራዊትንና የሰማይ ወፎችን ሁሉ፦ ሕያው ነፍስ ላለውም ሁሉ ስም ያወጣላቸው ዘንድ ወደ አዳም አመጣቸው። ይላል። ሂደቱም እንደሚከተለው ነው። እግዚአብሔር ዓርብ በነግህ አዳምን ከፈጠረ በኋላ ቅዳሜ መፍጠሩን ተወ። እሑድ እንስሳትን አራዊትን አመጣለት ፤ ሰኞ ማክሰኞ አዕዋፋትን አመጣለት፤ ረቡዕ በየብስ የተጠፈጠሩ ፍጥረታትን አመጣለት፤ ሐሙስ በባሕር የተፈጠሩ ፍጥረታትን አመጣለት፤ ለሁሉም ስም አወጣላቸው። በዚህን ጊዜ አዳም፦ ሁሉም ተባዕትና አንስት (ወንድና ሴት) መሆናቸውን አይቶ ፦ « ከእኔ በቀር ብቻውን የተፈጠረ የለም፤» ብሎ አዘነ። «ነገር ግን ለአዳም እንደ እርሱ ያለ ረዳት አልተገኘለትም ነበር ፤» ይላል።
፪ ፥፩ ፦ ሐዘነ አዳም፤
         እግዚአብሔር አዳም እስኪያዝን የጠበቀው ያለ ምክንያት አይደለም። አጭቶ፥ ወድዶ፥ ፈቅዶ እንዲገባበት ነው። ይህም፦ ወደፊት ሔዋን ስታሳስተው ለኃጢአቱ እግዚአብሔርን ምክንያት እንዳያደርግ ይጠብቀዋል። አዳም ሳያዝን ሔዋንን ፈጥሮለት ቢሆን ኖሮ፦ « ይኼ እግዚአብሔር ፍጠርልኝ ሳልለው ሔዋንን ፈጥሮ ምክንያተ ስሕተት ሆነችብኝ፤» ባለ ነበር። እግዚአብሔር ግን አዳም እስኪፈልግ ጠብቆ ፦ ከጎኑ አንዲት አጥንት ወስዶ ሴት አድርጎ ሠራለት። አዳምም፦ «ይህች አጥ ንት ከአጥንቴ ናት ፥ ሥጋም ከሥጋዬ ናት፤ እርስዋ ከወንድ ተገኝታለችና ሴት ትባል። ስለዚህ ሰው አባቱንና እናቱን ይተዋል፥ ከሚስቱም ይጣበቃል፤ ሁለቱም አንድ ሥጋ ይሆናሉ።» ብሎ እግዚአብሔር የሰጠውን በጸጋ ተቀበለ። ዘ፪፥፲፰-፳፬።