Wednesday, December 25, 2013

"አቡነ ተክለሃይማኖት ሐዋርያ" በዲ/ን ዳንኤል ክብረት



በዲ/ ዳንኤል ክብረት ስለ አባታችን ጻድቅ "አቡነ ተክለሃይማኖት ሐዋርያ" በሚል የተሰጠ መንፈሳዊ ትምህርተ ወንጌል፥ አይተው፣ ሰምተውና አዳምጠው፤ ስጋዎትንና ነፍሶትን ይመግቡ ዘንድ በእግዚአብሔር ስም ተጋብዘዋል።

በዚህ ትምህርት ውስጥ፦

* በዮዲት ጉዲት፥ የጥፋት ጊዜ፣ ለኢትዮጵያ ቤተ-ክርስቲያን የሚመጡ የነበሩ የግብፅ ጳጳሳት እንደቀሩና ክርስቲያን አማኞች የጠፉበት ጊዜ፤ እንደነበረ ይገልፅልናል።

* ዮዲት ጉዲት፥ አርባ ዓመታት ያህል፣ ታላቅ መከራና ከባድ ጥፋት ካደረሰች በኋላ፤ ባደረሰችው የቤተ-ክርስቲያን ብዝበዛ፣ ካህናትና ምዕመናን በጠፉበት ጊዜ፤ ከአንድ ትውልድ ጥፋት በኋላ፤ ፀሐየ ጽድቅ አቡነ ተክለሃይማኖት የተወለዱበትና የተነሱበት ጊዜ፤ ለኢትዮጵያ ቤተ-ክርስቲያን በጣም አስፈላጊ እንደሆነ፤ ወንድማችን ዳንኤል ክብረት፥ አልምቶና አብራርቶ ያስተምራል።

* በዚያን ግዜ፥ በመረጃ ያለመኖርና መለዋወጥ በማይቻልበት ወቅት፣ የግብፅ እስላሞች "ጳጳስ ነን" ብለው የመጡበት ጊዜ እንደነበረም ያትታል።

* በወቅቱ የነበረውን የኢትዮጵያን ታሪክ፣ ከዛም በኋላ የነበረውን የሃገሪቱን ታሪክና ሁናቴን፣ የቤተ-ክርስቲያን ታሪክ ይተርክልናል።

* አጠቃላይ፥ ስለ ፀሐየ ጽድቅ አቡነ ተክለሃይማኖት ተጋድሎና ሐዋርያዊ አገልግሎታቸውን በስፋት ያስቃኘናል።





ለወንድማችን / ዳንኤል ክብረት፥ እግዚአብሔር አምላክ የአገልግሎቱን ጊዜውን ይባርክለት፤ አሜን!

Tuesday, December 24, 2013

"የክርስቶስ የሆኑትን ጠልቶ የክርስቶስ መሆን የለም"


          "የክርስቶስ የሆኑትን ጠልቶ የክርስቶስ መሆን የለም" (ታምራት ፍሥሐ) የሚለውን ይህንን ድንቅ አባባል ሳነበው እጅግ መሰጠኝና የአባባሉን ፍሬ-ነገር ሳይለቅ፤ ይህቺን አጭር ጹሑፍ እንድጽፍ እግዚአብሔር መንፈን ቅዱስ አነሳሳኝ።

"የክርስቶስ የሆኑትን ጠልቶ የክርስቶስ መሆን የለም" እንዴት ያለ እጅግ እጹብ ድንቅና ምርጥ አባባል ነው። የክርስቶስ የሆኑትማ፥ እንደ ቅድስት ኤልሳቤጥ፦ "የጌታዬ እናት ወደ እኔ ትመጣ ዘንድ እንዴት ይሆንልኛል?" ብለው ያመሰግኗታል፣ እንደ ቅዱስ ገብርኤልም በትህትና ቃል በማክበር፥ "ደስ ይበልሽ፥ ጸጋ የሞላብሽ ሆይ፥ ጌታ ከአንቺ ጋር ነው፤ አንቺ ከሴቶች መካከል የተባረክሽ ነሽ" ይላታል። /ሉቃ 128 እና 43 /

ገና በእናታች ማህፀን ሳለን ጀምሮ የእመቤታችንን ሥሟንና ድምጿን መስማት ለሕይወታችን እንደሚያስፈልገን ለማንም ግለፅ ነው። ለምን ቢሉ? የክርስቶስ ከሆኑት አንዱ መጥምቀ ዩሐንስን እጠራላቸዋለን። እነሆ፥ የቅድስት ድንግል ማርያምን የሰላምታ ድምጽ  በቅድስት ኤልሳቤጥ ጆሮ በመጣ ጊዜ ፅንሱ በማኅፀኗ በደስታ እንደዘለለ፤ ተመዝግቦልናልና! /ሉቃ 144/

እናቶቻችን ባረገዙ (ነፍሰ-ጡር) ጊዜያት ስለ እመቤታችን ድንግል ማርያም፥ የተፃፉ መንፈሳዊ መፅሐፍትን፣ የተዘመሩ ዝማሬዎችን፤ እንዲሁም ደግሞ ሥሟንና ድምጿን ቢሰሙ ታደለዋል። አሁንም፥ ለምን ቢሉ? በቅድስት ኤልሳቤጥም መንፈስ ቅዱስ እንደሞላባት፥ እንነግራቸዋለን። አሁንም፥ እንቀጥላለን ስለ እመቤታችን፤ የስድብ ቃል ያይደለ፣ በመንፈስ ቅዱስ ምሪት መሰረት ታመሰግናታለህ። እንዲህ እያልክ "አንቺ ከሴቶች መካከል የተባረክሽ ነሽ" ትላታለህ። /ሉቃ 142/

ምን ይሄ ብቻ፥ የሃገሬ ሠውም ነፍሰ-ጡር የሆኑ እናቶቻችን በመክበብ፤ ማርያም፥ ማርያም፣ በማለት ድንግል ማርያምን ይጠሯታል። እመቤታችንም የጭንቅ አማላጅ ናትና ምጡ ሳይጠና ልጁ ይወለዳል።

ለምን ቢሉ? ስለ እናታችን እመ ብርሃን፣ ቅድስት ድንግል ማርያም ክብሯንና ጸጋዋን ጠንቅቆ የተረዳ ሁሉ፤ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም፥ ከፈጸመቻቸው ከመንፈሳዊ ምግባራት፣ ከብዙዎች አንዱ የሆነውን፤ በተራራማው አገር ፈጥና ወደ ይሁዳ ከተማ የተጓዘችበትን መንፈሳዊ ጉዞ በማስታዎስ፥ ለቅድስት ድንግል ማርያምና ለልጇ ዕልልታና ምስጋና ያቀርባሉ፤ ከዚያም የወለደችውን እናት "ማርያም፥ ከሽልም ታውጣሽ" ይሏታል። /ሉቃ 139/

ሌላው ደግሞ የክርስቶስ ከሆኑት አንዱ፥ ቅዱስ ዮሐንስ በአንደኛ ክታቡ ላይ "ትእዛዝን ከአብ እንደ ተቀበልን ከልጆችሽ በእውነት የሚሄዱ አንዳንዶችን ስለ አገኘኋቸው እጅግ ደስ ብሎኛል። አሁንም፥ እመቤት ሆይ፥ እርስ በርሳችን እንድንዋደድ እለምንሻለሁ።"/2 ዮሐ 14-5/ ይላል።

ታዲያ፥ ትእዛዝን ከአብ እንደሆነ ሁሉ፤ በልጇ በኢየሱስ ክርስቶስ፥ በተገኙት ሐዋርያት፣ ቅዱስ ዮሐንስ እጅግ ደስ ካሰኘው፣ "እመቤት" ብሎ በጠራት በእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም የመዋደድና አንድ የመሆን ፍላጎት እንዲኖረን "እመቤት ሆይ፥ እርስ በርሳችን እንድንዋደድ እለምንሻለሁ።" ካለ፤ የእግዚአብሔር ወዳጆች ሆይ፦ እኛ፥ የቅዱስ ዮሐንስን ደስታንና ልመናውን፤ አጥብቀን እንፈልግ እንጂ!!!

"የክርስቶስ የሆኑትን ጠልቶ የክርስቶስ መሆን የለም!" በተጨማሪም፥ በእግዚአብሔር ፈቃድ የኢየሱስ ክርስቶስ ሐዋርያ ሊሆን የተጠራ ቅዱስ ጳውሎስ፤ እንዲህ ይለናል፦ "በእግዚአብሔር ቅንዓት እቀናላችኋለሁና፥ እንደ ንጽሕት ድንግል እናንተን ለክርስቶስ ላቀርብ ለአንድ ወንድ አጭቻችኋለሁና" /2 ቆሮ 112/ ብሎናል። እናም፥ ንጽሕት ድንግል ለክርስቶስ ብቻ የቀረበች ናት፣ ለእርሱ ለራሱ ብቻ የታጨች መሆኗን ሐዋርያ አስረግጦ አስረዳን! በዚህም ላይ ሐዋርያ ቅዱስ ጳውሎስ እኛን እንደ ንጽሕት ድንግል ለክርስቶስ አቅርቦንና አጭቶን (እንዳጨን) ነግሮናል።

በቃ! ንጽሕት ድንግል ለክርስቶስ ብቻ የቀረበች ናት፣ ለእርሱ እና ለራሱ ብቻ የታጨች፤ እመቤታችን ብቻ ናት!!!

Monday, December 23, 2013

ፍቅሬ ሆይ፦


ፍቅሬ ሆይ፥ ቀኑን ሙሉ ሳስብሽ እውላለሁ፤
እንቅልፍ እየነሳኝ ... ሌሊት ሌሊት እባንናለሁ። 

 
ከመኝታዬ ተንስቼ ... መስኮቴን ከፍቼ፤
ፊቴን ... ሽቅብ ወደ ላይ አንጋጥቼ፤
ዓይኖቼን ... ወደ ሠማዩ አንስቼ፤
ጨረቃዋን ... አትኩሬ ተመልክቼ።


የኮከቦች ድምቀት ... በድቅድቅ ጨለማ፤
ከአድማስ አድማስ ... መድረሷማ፤
ብልጭ ድርግም ... ማለቷማ፤
ልዩ ናት አቀማመጧ ... ጨረቃ ውበቷማ።

ጎህ ሲቀድ ... ጨረቃዋ ስትርቅ፤
የሌሊቱ ቅዝቃዜ ... ለማራቅ፤


ቀረበች ፀሐይ ... ምድርን ለማሸብረቅ፤
ዓለምን ... በብርሃኗ ለማሞቅ።

በጨረቃዋ ፍንጣቂ ... ፍቅሬን እንዳያዋት፤
ከሌሊቱ ይልቅ ... ወዳጄን እጅግ ፈለኳት፤
በፀሐይ ጮራ ውስጥ ... በጧት ፍካት፤
ፊቴ በብርሃን ተሞላ ... ፍቅሬን ስላየዋት።

ጨረቃ፥ ለፀሐይ ቦታዋን ... እንደለቀቀች፤
ፍቅሬን በማየቴ ... ልቤ ሐሴት ተሞላች።

ፍቅሬ ሆይ፥ ... ቀኑን ሙሉ ሳስብሽ እውላለሁኝ፤
እንቅልፍ እየነሳኝ ... ሌሊት ሌሊት እባንናለሁኝ።
የኔ ፍቅር፥ ... እወድሻለሁ፣ አፈቅርሻለሁኝ፤
ይህቺን ሌሊት .. ልደግማት እናፍቃለሁኝ።

ከሥንታየሁ ጌታቸው (ታኅሣስ ፲፩/ ፪፻፮ /)