Showing posts with label ነገረ ክርስቶስ. Show all posts
Showing posts with label ነገረ ክርስቶስ. Show all posts

Saturday, April 11, 2015

ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ፦ የቤተክርስቲያን ትምህርት፤ (ክፍል ፬) መልአከ ሰላም ቀሲስ ደጀኔ ሺፈራው


          በስመአብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን።

                                                                      (ክፍል ፫ ለማንበብ እዚህ ይጫኑ)
 

ቅዳሴ ማርያምን በመንፈስ ቅዱስ ምሥጢር ገላጭነት የደረሰ አባ ሕርያቆስ ዘሀገረ ብህንሳ ነው። ሕርያቆስ ማለት፦ ለሹመት መርጠውታልና፥ ኅሩይ (ምርጥ) ማለት ነው። አንድም፦ ረቂቅ ምሥጢረ ሥላሴን ይናገራልና፥ ረቂቅ ማለት ነው። እርግጥ ከሊቃውንት ምሥጢረ ሥላሴን ያልተናገረ ባይኖርም፥ እርሱ አምልቶ አስፍቶ ተናግሯል። አንድም፦ አብ ፀሐይ፥ ወልድ ፀሐይ፥ መንፈስ ቅዱስ ፀሐይ ብሎ ጽፏልና ፀሐይ ማለት ነው። አንድም፦ የምዕመናንን ልቡና በትምህርቱ ብሩኅ ያደርጋልና፥ ብርሃን ማለት ነው። አንድም፦ ንብ የማይቀስመው አበባ እንደሌለ፥ እርሱም የማይጠቅሰው ሊቅ የለምና ንብ ማለት ነው።

ሹመትን በተመለከተ፥ ቅዱሳን ሐዋርያት፦ በትምህርቱ መናፍቃንን ተከራክሮ ይረታ ዘንድ የተማረ ይሾም፤ ይህም ባይሆን በጸሎቱ ስለሚጠብቅ፥ በትሩፋቱ ስለሚያጸድቅ፥ ባይማርም ግብረ ገብ የሆነ ሰው ይሾም ብለዋል። ይኸውም ትህትናው እስካለ ድረስ ውሎ አድሮ ተምሮ ምሥጢር ያደላድላል ብለው ነው። በዚህ መሠረት አባ ሕርያቆስ ትምህርት ባይኖረውም ግብረ ገብነት ነበረውና እልፍ መነኮሳትና እልፍ መነኮሳይት መርጠውታል። ግብረ ገብ በመሆኑም ሥርዓት ስላጸናባቸው መልሰው ጠልተውታል፥ ትምህርት ስላልነበረውም ንቀውታል። ከዕለታት በአንዳቸው ቀን በምን ምክንያት እንደሚሽሩት አስበው፥ «ቀድሰህ አቊርበን፤» አሉት። ትምህርት ስለሌለው አይሆንለትም ብለው በተንኰል ነው።

የአባ ሕርያቆስ ተምኔቱ (ምኞቱ) እንደ ቅዱስ ኤፍሬም፥ የእመቤቴ ምስጋና፦ እንደ ባሕር አሸዋ፥ እንደ ሰማይ ኮከብ በዝቶልኝ፥ እንደ ምግብ ተመግቤው፥ እንደ መጠጥ ጠጥቼው፥ እንደ ልብስ ለብሼው የሚል ነበር። የጠሉት እና የናቁት ሊቃውንት፥ «ከሊቃውንት ቅዳሴ የሚያስቸግረውን የቱን እናውጣለትእያሉ፥ በኅሊናቸው ሲያወጡ ሲያወርዱ፥ ሥርዓተ ቅዳሴውን ጨርሶ ከፍሬ ቅዳሴ ደረሰ። በዚህን ጊዜ፦ የለመኗትን የማትነሳ፥ የነገሯትን የማትረሳ እመቤት ገልጣለት «ጐሥዓ ልብየ ቃለ ሠናየ ከሚለው አንሥቶ፥ ወይእዜኒ ንሰብሖ ለአብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ፤» እስከሚለው ድረስ ሰተት አድሮጎ ተናግሮታል።

ብፁዕ አቡነ ቀውስጦስ፦ «ክፉ ሰው የሚለውን አያጣም፤» እንዳሉ፥ እነዚያ የሚጠሉትና የሚንቁት ሊቃውንት፦ «ይህ፦ የተናገሩትን ቀለም እንኳ አከናውኖ መናገር የማይቻለው፥ ዛሬስ እንግዳ ድርሰት እድርሳለሁ ብሎ አገኝ አጣውን ይቀባጥራል፤» ብለው አጣጣሉበት። የሚወዱት እና የሚያከብሩት ግን፦ «እንዲህ ያለ ምሥጢር ከመንፈስ ቅዱስ ነው እንጂ ከእሩቅ ብእሲ የሚገኝ አይደለም፤» ብለው አጸደቁለት። በዚያውም ላይ «ጽፈን ደጉሰን እንያዘው፤» አሉ። የጠሉት ግን ከንቀታቸው ብዛት «ማን ተናገረው ብለን እንይዘዋለንብለው ተቃወሙ። የሚወዱትና የሚያከብሩትም መልሰው «እንደ ልማዱ አድርገን አንይዘውምንአሉ። በሀገራቸው ልማድ እንግዳ ድርሰት የተደረሰ እንደሆነ፥ ጽፈው ደጉሰው ከእሳት ይጥሉታል፥ ከእሳት ደህና የወጣ እንደሆነ ከውኃ ይጥሉታል፥ ከውኃ ደህና የወጣ እንደሆነ ከሕሙም ላይ ይጥሉታል፥ ታማሚውን የፈወሰው እንደሆነ ደገኛ ድርሰት ነው ብለው ይይዙታል። የአባ ሕርያቆስንም ድርሰት ከእሳት ቢጥሉት በደህና ወጣ፥ ከውኃ ቢጥሉት በደኅና ወጣ፥ ከሕሙምም ላይ ቢጥሉት ፈወሰው፥ ይልቁንም ሙት አንሥቷል። በዚህን ጊዜ ደገኛ ድርሰት ነው ብለው አሥራ አራተኛ ቅዳሴ አድርገው ጠርዘውታል። አባ ሕርያቆስ በዚህ ድርሰቱ ያልተናገረው ምሥጢረ ሃይማኖት የለም። ምሥጢረ ሥላሴን፥ ምሥጢረ ሥጋዌን፥ ምሥጢረ ጥምቀትን፥ ምስጢረ ቊርባንን፥ ምሥጢረ ትንሣኤ ሙታንን አምልቶ አስፍቶ ተናግሯል።

ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ፦ የቤተክርስቲያን ትምህርት፤ (ክፍል ፫) መልአከ ሰላም ቀሲስ ደጀኔ ሺፈራው


        በስመአብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን።

          ፪፦ በውዳሴ ማርያም ትሰብከዋለች። (ካለፈው የቀጠለ . . . ክፍል ፪ ለማንበብ እዚህ ይጫኑ)

 ፪፥፫፦ ነፃነትን ሰበከላቸው

      አባታችን አዳምና እናታችን ሔዋን በግብርናተ ዲያብሎስ ተይዘው (የዲያብሎስ ባሮች ሆነው) ለአምስት ሺህ አምስት መቶ ዘመን፥ እስከ ልጅ ልጆቻቸው በሲኦል ኖረዋል። ኑሮውም የሥቃይና የፍዳ ነበር፥ ይህም ያን ዘመን፥ ዘመነ ፍዳ፣ ዘመነ ኲነኔ አሰኝቶታል። ጊዜው ሲደርስ (እግዚአብሔር፦ አምስት ቀን ተኲል ሲፈጸም፥ ከልጅ ልጅህ ተወልጄ አድንሃለሁ ብሎ ለአዳም የገባው ቃል የሚፈጸምበት ዘመን ሲደርስ) ከሦስቱ አካላት አንዱ ወልድ፥ በተለየ አካሉ ከሰማየ ሰማያት ወርዶ ከድንግል ማርያም ተወለደ። ቀስ በቀስ አድጎ በሠላሳ ዓመቱ ተጠመቀ፥ ሦስት ዓመት ከሦስት ወር ወንጌልን አስተማረ፥ ተአምራትንም አደረገ፥ በመጨረሻም በዕፀ መስቀል ተሰቅሎ (ሥጋውን በመቁረስ፥ ደሙን በማፍሰስ፥ ነፍሱንም በፈቃዱ አሳልፎ በመስጠት) የሰውን ልጅ አዳነ። በአካለ ሥጋ ወደ መቃብር ወርዶ ሙስን መቃብርን አጠፋ፥ በአካለ ነፍስ ደግሞ ወደ ሲኦል ወርዶ ነፍሳትን ማረከ፥ ሲኦልን ባዶ አስቀረ። ይኽንንም ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ፦ «ክርስቶስም ስለ ሰው ኃጢአት አንድ ጊዜ ሞቷልና፤ ጻድቅ እርሱ እኛን ወደ እግዚአብሔር (ወደ ባሕርይ አባቱ ወደ አብ፥ ወደ ራሱ እና ወደ ባሕርይ ሕይወቱ ወደ መንፈስ ቅዱስ) ያቀርበን ዘንድ ስለእኛ ስለ ኃጢአታችን በሥጋ ሞተ፤ (በተለየ አካሉ በተዋሕዶ ሰው ኹኖ ሞተ) በመንፈስ ግን (በመለኰት) ሕያው ነው። በእርሱም (ሥጋን ተዋሕዶ በአካለ ሥጋ ወደ መቃብር እንደወረደ፥ ነፍስንም ተዋሕዶ በአካለ ነፍስም) በወኅኒ (በሲኦል) ወደአሉ ነፍሳት ሄዶ ነጻነትን ሰበከላቸው።» በማለት ገልጦታል። ፩ኛ ጴጥ ፫፥፲፰-፲፱። ይኽንን ታላቅ የነገረ ድኅነት ምሥጢር ይዘን ወደ ውዳሴ ማርያም ስንሄድ፦ «ፈቀደ እግዚህ ያግዕዞ ለአዳም ኅዙነ ወትኩዘ ልብ ወያግቦዖ ኀበ ዘትካት መንበሩ፤ ጌታ ልቡ ያዘነና የተከዘ አዳምን ነፃ ያወጣውና ወደ ቀድሞው ቦታው (ወደ ጥንተ ርስቱ ገነት) ይመልሰው ዘንድ ወደደ፤» ይለናል። (የሰኞ . ) በተጨማሪም፦ «በዳዊት አገር የተወለደ መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አዳምንና ሔዋንን ነፃ አደረጋቸው፤» እያለ ይሰብከናል። (የሰኞ . )

   ፪፥፬፦ ጌትነቱ፥ አካላዊ ቃልነቱ፥ አምላክነቱ፥ ልጅነቱና ስሙ

      በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን፦ ነገረ ክርስቶስ (ምሥጢረ ድኅነት) ከስብከት አልፎ ጸሎት፥ መዝሙር፥ ቅዳሴ፥ ማኅሌት ሆኗል። የሰባቱን ዕለታት ውዳሴ ማርያም በግዕዝም ሆነ በአማርኛ የምንደግም (የምንጸልይ) ሰዎች፥ እግዚአብሔር የሚለውን ስም ሠላሳ አምስት ጊዜ፥ ጌታ የሚለውን ሃያ አንድ ጊዜ፥ ኢየሱስ ክርስቶስ የሚለውን ሠላሳ ሰባት ጊዜ፥ መድኃኒት የሚለውን ሠላሳ ሰባት ጊዜ፥ አማኑኤል የሚለውን አምስት ጊዜ፥ መለኮት የሚለውን ዘጠኝ ጊዜ፥ ንጉሥ የሚለውን ዘጠኝ ጊዜ፥ ፈጣሪ የሚለውን አራት ጊዜ፥ ብርሃን የሚለውን አሥራ አራት ጊዜ፥ ሕይወት የሚለውን አምስት ጊዜ እንጠራለን። ኃይለ ቃሉ ትርጓሜው እና ምሥጢሩ በትክክል ነገረ ድኅነትን የሚሰብክ፥ ቀራንዮን የሚያሳይ ነው።