Tuesday, August 6, 2013

እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም (ክፍል ሁለት)

በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ሺኖዳ


ቤተክርስቲያን እመቤታችንን የምታከብርበት አስፈላጊና ዋና ዋና ምክንያቶች

1.        መንፈስ ቅዱስ ስለጸለላት /መንፈስ ቅዱስ በርሷ ላይ ስለሆነ/፣
2.      የእግዚአብሔር እናት /እመአምላክ ስለሆነች/፣
3.      ዘለማዊ ድንግል ስለሆነች፣
4.      ቅድስት ስለሆነች፣
5.      መንፈስ ቅዱስ ስለመሰከረላት፣
6.     ጌታ ራሱ ስላከበራት፤
7.      ስለ ተአምራቷና ስለተቀደሰው መታየቷ ናቸው። ይህም /በተለያየ ጊዜያት/ በግብጽ የመገለጽ ክብር ነው።

ክብሯም፦ በቤተክርስቲያን ንዋየቅዱሳት፣ በመዝሙራት፤ በቤተክርስቲያን ጸሎት ምልጃዋን በመለመን በዓላቷን በማክበር እና አንዱን ጾማችን በስሟ በመጾማችን ይገለጣል።


የእመቤታችን በዓላት

1.        ጥር 21 ቀን ያረፈችበት ነው በሁሉም ወራት 21ኛ ቀን ትከበራለች፣
2.      ነሐሴ 7 ቀን የተጸነሰችበት ነው፣
3.      ግንቦት 1 ቀን የተወለደችበት ነው፣
4.      ታህሳስ 3 ቀን ወደ ቤተመቅደስ የገባችበት ነው፣
5.      በግንቦት 24 ቀን ወደ ግብጽ የገባችበት ነው፣
6.     የካቲት 16 ቀን ተዝክሯን ላደረገና ስሟን ለጠራ ልጇ የምህረት ቃለ ኪዳን የሰጠበት ቀን ነው፣
7.      ሰኔ 21 ቀን በፊልጲያ በስሟ የተሰራውን ቤተክርስቲያን ልጇ ያከበረበት ነው፤
8.      መጋቢት 24 ካይሮ በሚገኘው በዘይቱን ቤተክርስቲያና የታየችበት ነው።

በእመቤታችን ስሞች ላይ ያሉ ሁለት ጥያቄዎች

1. ክርስቶስ “እውነተኛ የወይን ግንድ እኔ ነኝ ገበሬውም አባቴ ነው፤ እኔ የወይን ግንድ ነኝ እናንተ ቅርንጫፎች ናቹሁ።” /ዮሐ 15፥1እና5/ እያለን ሳለ እኛ ታዲያ በሦስተኛው ሰዓት ጸሎታችን ለምን «የአምላክ እናት ሆይ አንቺ የህይወትን ፍሬ የተሸከምሽ እውነተኛ ወይን ነሽ» ለምን እንላታለን?
   
2. ክርስቶስ “እውነት እውነት እላችኋለሁ እኔ የበጎች በር ነኝ።” /ዮሐ 10፥7/ እያለን እመቤታችን በእኩለ ሌሊት ጸሎታችን የህይወት በር ሆይ ብለን ለምን እንጠራታለን? 

             እመቤታችን የወይን ሐረግ ናት፥ ቤተክርስቲያንም ሐረገወይን ትላታለች

እመቤታችንን እውነተኛ ወይን ብሎ መጥራት እውነተኛ ወይን ከሚለው ከጌታችን ስም ጋር በምንም መንገድ አይጋጭም። ጌታ እውነተኛ ወይን እንደሚባለው ሁሉ እመቤታችንም እውነተኛ ወይን ትባላለች፥ እኛ ቅርንጫፎቹ ስንሆን ጌታ ወይን ነው፣ እርሱ የመጀመርያ ሲሆን እኛ ከእርሱ ተገኘን፣ እርሱ እራስ ነው፤ እኛ ሁላችን ደግሞ የተለያዩ አካላት ክፍሎች ነን። እመቤታችን የህይወት ፍሬ የወለደችልን ነች፥ እርሷ በአካልም በህሊናም የሰው ለማድ ያልደረሰባት ወይን ነች። እዚህ ላይ ዋናው ነጥብ ልንመዘግብ እንወዳለን፤ ጌታችን እየሱስ ክርስቶስ ጥቂት ስሞቹን ሰጥቶናል።

1.        ጌታ “እኔ መልካም እረኛ ነኝ” ዮሐ 10፥11እና14/ አለ፤ ይህም ቀደም ብሎ በቅዱስ ዳዊት ለእግዚአብሔር ተሰጥቶ ነበር “እግዚአብሔር እረኛዬ ነው” /መዝ 22፥11/ ሕዝቅኤልም ይህንኑ ደግሞታል /ሕዝ 34፥11-16/ ይመልከቱ። ጌታ ቤተክርስቲያንን ሲመሰርት “አንድ መንጋ ይሆናሉ እረኛውም አንድ” /ዮሐ 10፥16/ አለ፤ ሆኖም ግን ራሱ ጥቂት ልጆቹን እረኞች ብሎ ሰይሟል፣ ለሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ “የዮና ልጅ ስምዖን ሆይ፥ ከእነዚህ ይልቅ ትወደኛለህን? አለው። አዎን ጌታ ሆይ፥ እንድወድህ አንተ ታውቃለህ አለው። ግልገሎቼን አሰማራ አለው፤ ጠቦቶቼን ጠበቅ... በጎቼን አሰማራ አለው።” /ዮሐ 21፥15-17/

1.1     በብሉይ ኪዳንም “እንደ ልቤም በግ ጠባቂዎችን እሰጣችኋለሁ፥ በእውቀትና በማስተዋልም ይጠብቋችኋል።” /ኤር 3፥15/ አለ ጌታ። እረኛ የሚለው ስም ለሐዋርያት ተከታዮች ለጳጳት የተገባ ሆነ። ይንንም ሲገልጥ፦ “በገዛ ደሙ የዋጃትን የእግዚአብሔርን ቤተ ክርስቲያን ትጠብቁአት ዘንድ መንፈስ ቅዱስ እናንተን ጳጳሳት አድርጎ ለሾመባት ለመንጋው ሁሉና ለራሳችሁ” /ሐዋ 20፥28/  “የእግዚአብሔርን መንጋ ጠብቁ” /1ኛ ጴጥ 5፥2/ አለ።

2.      ኢየሱስ ክርስቶስ እራሱን ብርሃን ብሎ ይጠራል “እኔ የዓለም ብርሃን ነኝ” /ዮሐ 8፥12 ፣ 9፥5/ ሆኖም ሐዋርያቱን “እናንተ የዓለም ብርሃን ናችሁ።” /ማቴ 5፥14/ እንዲሁም “ብርሃናችሁ በሰው ፊት ይብራ” /ማቴ 5 16 አላቸው።

2.1    ጌታ ፍጹም ብርሃን መሆኑ ጥርጥር የለውም፣ በተጨማሪ ደቀመዝሙርቱ ብርሃን ናቸው። ምክንያቱም ከእርሱ ብርሃን አግኝተዋለና በእርሱ ብርሃን በሰው ፊት ያበራሉ። በተመሳሳይ ሁኔታ እርሱ ፍጹም እረኛ ነው፥ እነርሱም እንደዚሁ እረኞች ናቸው። ምክንያቱም መንጋውን እንዲጠብቁ የተሾሙ የእግዚአብሔር እንደራሴዎች ስለሆኑ ነው።

3.      ስለጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ “የነፍሳችሁ እረኛና ጠባቂ” /1ኛ ጴጥ 2፥25/ ተብሏል፣ ሆኖም የሐዋርያት ደቀመዝሙርት እረኞች (ጳጳሳት) ሆነው በመንፈስ ቅዱስ ተሾመዋል።

4.      ስለጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ “አንተ እንደ መልከ ጼዴቅ ሹመት ለዘለዓለም ካህን ነህ።” /መዝ 109፥4 ዕብ 5፥6/ ተብሏል። ነገር ግን ስለ ሊቃነ-ካህናት እና ስለ ካህናት እግዚአብሔር ዘለዓለማዊ ክህነት እንደሰጠው የሚያስረዱ ብዙ ጥቅሶች በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ አሉ። /ዘፀ 40፥15/ በብሉይ ኪዳን “ካህናቶችህ ቅዱሳንህም ደስ ይበላቸ፤ ... ካህናቶቿም ደህንነት (ጽድቅን) አለበሳቸዋለሁ።” /መዝ 132፥9እና16/ “ከቅባቱም ዘይት በአሮን እራስ ላይ አፈሰሰ ይቀድሰውም ዘንድ ቀባው።” /ዘሌ 8፥12/ እና “የተቀደሰውንም ልብስ ለክብርና ለጌጥ እንዲሆን ለወንድምህ ለአሮን ስራለት።”/ዘፀ 28፥2/ ተብሎ ተጽፏል።

4.2  በአዲስ ኪዳን ቅዱስ ጳውሎስ ራሱን ካህን ብሎ ሲጠራ እናነባለን። “እንደ ካህን እያገለገልሁ” /ሮሜ 15፥16/ ኢየሱስ ክርስቶስ ራሱን ስለእኛ መስዋዕት ያደረገ ካህን ነው፣ ነገር ግን የሰው ልጆች የሆኑ ካህናት፤ አገልጋዮችና የእግዚአብሔር እንደራሴዎች ናቸው።  የእግዚአብሔርን ምስጢር የክርስቶስን መስዋዕት ያቀርባሉ፣ እርሱም ስጋውና ደሙ ነው፤ በብሉይ ኪዳን ደግሞ የክርስቶስን ምሳሌ የሆነውን ያቀርቡ ነበር።

5.      ክርስቶስ የእግዚአብሔር ልጅ እንደሆነ ተጽፏል፦ “እኛም አይተናል አባትም ልጁን የዓለም መድኃኒት ሊሆን እንደ ላከው እንመሰክራለን። ኢየሱስ የእግዚአብሔር ልጅ እንደ ሆነ በሚታመን ሁሉ እግዚአብሔር በእርሱ ይኖራል እርሱም በእግዚአብሔር ይኖራል።” /1ኛ ዮሐ 4፥14-15/ እኛም ደግሞ የእግዚአብሔር ልጆች ነን። “የእግዚአብሔር ልጆች ተብለን ልንጠራ አብ እንዴት ያለውን ፍቅር እንደ ሰጠን እዩ፥ እንዲሁም ነን።” /1ኛ ዮሐ 3፥1/

ወይን” የሚለው ስምም እንዲሁ ነው

ኢየሱስ ክርስቶስ ወይን ነው፣ ቤተክርስቲያን ደግሞ የወይን ቦታ ነች፣ በኢሳያስ መጽሐፍ ስለ ወይን ቦታው ስለ ቤተክርስቲያን ይዘምራል፤ “አሁንም እናንተ በኢየሩሳሌም የምትኖሩ የይሁዳ ሰዎች ሆይ፥ በእኔና በወይኑ ቦታዬ መካከል እስኪ ፍረዱ። ...የሠራዊት ጌታ የእግዚአብሔር ወይን ቦታ እርሱ የእስራኤል ቤት ነው።” /ኢሳ 5፥3እና7/ ይላል።

ጌታችን “የወይን አትክልት የተከለ ባለቤት ሰው ነበረ፤ ቅጥርም ቀጠረለት፥ መጥመቂያም ማሰለት፥ ግንብም ሠራና ለገበሬዎች አከራይቶ ወደ ሌላ አገር ሄደ።” /ማቴ 21፥33-41/ በማለት ስለወይን ቦታውና ስለጠባቂዎቹ የተናገረውም ከዚሁ ጋር ተመሳሳይ ነው፣ በዚህ ገለጻ የወይኑ ቦታ ቤተክርስቲያን፣ ጠባቂዎቹ ካህናት፣ የወይኑ ባለቤት ደግሞ እግዚአብሔር ነው።

ቤተክርስቲያንን «ወይን» ብሎ ስለ መጥራቱ መለኮታዊ ቃሉን እንጠቅሳለን “የሠራዊት አምላክ ሆይ፥ እንግዲህ ተመለስ፤ ከሰማይ ተመልከት፥ እይም፥ ይህችንም የወይን ግንድ ጐብኝ።” /መዝ 80፥14/ ታዲያ ቤተክርስቲያንን «ወይን» ብንላት የእግዚአብሔርን ክብር ሰርቀነዋልን? ወይስ መጽሐፍ ቅዱስ “በዚያም ቀን ለተወደደው የወይን ቦታ ተቀኙለት፤ እኔ እግዚአብሔር ጠባቂው ነኝ፤” ... /ኢሳ 27፥2-3/ የሚላትን ቤተክርስቲያንን መቃወም ነውን? ከዚህም በላይ «ወይን» የሚለው ስም ለተባረከች እናት ሁሉ የሚሰጥ ስም ነው፣ ይህንንም ነቢዩ ዳዊት “ሚስትህ በቤትህ እልፍኝ ውስጥ እንደሚያፈራ ወይን ናት፤” /መዝ 128፥3/ በማለት ይገልጠዋል። ስለዚህም ቅድስት ድንግል ማርያምን «ወይን» ብሎ መጥራት የሚደንቅ አይሆንም።
ድንግል ማርያም የሕይወትና የድኀነት በር ነች

በመጽሐፍ ቅዱስ ድንግል ማርያም «በር» ትባላለች፣ በሕዝቃኤልም መጽሐፍ በምስራቅ ያለችና በር እግዚአበሔር የገባበትና እንደገባም የወጣበት ተብላ ተገልጻለች። “እግዚአብሔርም። ይህ በር ተዘግቶ ይኖራል እንጂ አይከፈትም፥ ሰውም አይገባበትም፤ የእስራኤል አምላክ እግዚአብሔር ገብቶበታልና ተዘግቶ ይኖራል።” /ሕዝ 44፥2/ አለ።

ጌታ ሕይወት እንደሆነ ድንግልም የሕይወት በር ነች፤ ጌታ ሕይወት መሆኑን “ኢየሱስም፦ ትንሣኤና ሕይወት እኔ ነኝ፤ የሚያምንብኝ ቢሞት እንኳ ሕያው ይኖራል፤” /ዮሐ 11፥25/ በማለት ተናገግሯል። ታዲያ ድንግል፥ ክርሰቶስ የመጣበት በር እንደመሆኗ እርሷ የሕይወት በር ነች። /ሉቃ 19፥10/ ጌታ አዳኝ ነው፥ እመቤታችንም የድኀነት በር ነች።

እመቤታችንን “የሕይወት በር” ብሎ መጠራት አያስደንቅም፣ ከብዙ ጊዜ በፊት ቤተክርስቲያን “በር” ተብላ ተጠርታለች፣ አባታችንም ያዕቆበም የተቀደሰችውን ሥፍራ (ቤተክርስቲያን) ቤቴል ብሎ ሰየማት፤ ይኸውም፦ የእግዚአበሔር ቤት ማለት ነው። ስለ እርሷም፦ ይህ ስፍራ እንዴት ያስፈራ፤ ይህ ስፍራ የእግዚአብሔር ቤት ነው እንጂ ሌላ አይደለም፤ ይህም የሰማይ ደጅ ነው። /ዘፍ 28፥17/


ይቀጥላል ...
---------------- ይቆየን!!!  --------------

ዋቢ፦ መጽሐፈ “አንጻራዊ ትምህርተ መለኮት”
{አዘጋጅ፦ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ሺኖዳ፤ ትርጉም፦ ያየህይራድ አስናቀ}













1 comment: