Friday, March 13, 2015

እንደገና ወደ ግብጽ መኼድ፦ ሊቀ ሊቃውንት አለቃ አያሌው ታምሩ



በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አመራር ላይ ከቅርብ ዓመታት ወዲህ በተደጋጋሚ የተከሰቱትን የሃይማኖት ትምህርትና የሥርዓት መበላሸት በማስመልከት የቤተ ክርስቲያኒቱ የሊቃውንት ጉባኤ ሰብሳቢ የነበሩት አለቃ አያሌው ታምሩ ችግሩ ሥር ሳይሰድ ገና ከጅምሩ እንዲታረም ማሳሰቢያና ተማጽኖ ለቤተ ክርስቲያኒቱ ቅዱስ ሲኖዶስ ተደጋጋሚ ተማጽኖ አቅርበው ነበር። ነገር ግን ጥያቄአቸው በቅዱስ ሲኖዶስ ዘንድ በቸልታ በመታየቱ ምክንያት፤ አለቃ አያሌው ታምሩ ባላቸው ከፍተኛ ሥልጣንና ኃላፊነት፤ በቤተ ክርስቲያን ላይ ዐመጽ የሚፈጽሙትን ፓትርያርኩንና ተከታዮቻቸውን ማውገዛቸው ይታወቃል። ቃለ ግዝታቸው በመጀመሪያ የወጣው ሰኔ ፳፯ ቀን ፲፱፻፹፰ / «መብሩክ» ጋዜጣ ላይ ነበር። ሙሉውን ቃለ ውግዘት ለማንበብ ከዚህ ይጫኑ

አባታችን ይህን ቃለ ውግዘት ካስተላለፉበት ጊዜ ጀምሮ፤ ከምእመናንና ከተለያዩ ክፍሎች ውግዘቱን አስመልክቶ የተለያዩ ጥያቄዎች በቃልና በጽሑፍ፥፣ እንዲሁም በተለያዩ ጋዜጦች ላይ የቀረቡላቸው ሲሆን፤ ለቀረቡት ጥያቄዎችም ተገቢ የሆኑ ምላሾችን ሰጥተዋል ሰጥተዋል። በተለያዩ ጊዜዎች ከቀረቡላቸው ጥያቄዎች መካከል በ፲፱፻፺ / ብዙ ምእመናን በመኖሪያ ቤታቸው ተገኝተው በጋራ ያቀረቡላቸው ሲሆን፤ ከእነዚህ ጥያቄዎች መካከል አንዱ "በዚህ ውግዘት መካከል በእርስዎ ወይም በሳቸው መካከል የመለየት ባሕርይ ቢኖር ውግዘቱ እንደ ታሰረ ነው ወይስ እንደ ተፈታ ነው የሚቆየው? ውግዘቱን ማን ይፈታዋል? እስከ መቼ ድረስ ነው ውግዘቱ የሚቆየው?" የሚል ሲሆን፤ ክቡር አባታችን የሚከተለውን ምላሽ ሰጥተው ነበር።

"ውግዘቱ እንደ ታሰረ ነው የሚቆየው፤ ማንም አይፈታውም። ቤተ ክርስቲያኒቱ እስከ ተመለሰች ድረስ ውግዘቱ ይቆያል። ቤተ ክርስቲያኒቱ ተመልሳ ሲኖዶሱ የቤተ ክርስቲያን፥ ክርስቶስ ተጠሪ ካልሆነ ምን ጊዜም አይፈታም። ክርስቶስ የሆኑ ጳጳሳት ከሌሉ፣ ካልተሾሙ፣ አሁን ያሉት ጳጳሳት አንዲያውም አይሆኑም፣ አሁን ያሉት አይሆኑም፣ ያሉት ካህናትም አይሆኑም፤ ይህን ዕወቁ። ለዚህ መድኃኒቱ ምእመናን ተሰብስበው ካህናቱንም አስገድደው፤ እሺ ያላቸውን በውድ፥ እምቢ ያላቸውን በግድ ለይተው አስወጥተው፤ አሁንም አባ ጳውሎስን አውግዘው፥ ራሳቸውን አስተካክለው ካልቆሙ በስተቀር ቤተ ክርስቲያን አሁንም የለችም፣ እንዲህ በመላም ደግሞ አትመለስም፣ ይህን ዕወቁ፤ በመላም አትመለስም። አባ ጳውሎስ ድንገት ቢሞቱ፥ እኔም ድንገት ብሞት፣ ያሉት ጳጳሳት፤ ያሉት ቀሳውስት ተተክተው የሚሠሩት ሥራ ምንም ዋጋ የለውም። ፍርድ ሳይፈረድ፥ አጥፊውና አልሚው ሳይለይ በምንም ዐይነት የሚደረገው ነገር ሁሉ ዋጋ የለውም። ለዚህ ነው የጮኽኩት፤ ዓመት ሙሉ የሰው ያለህ የምል በዚህ ምክንያት ነው። ነገሩ ጥብቅ ስለ ሆነ፥ ከባድ ስለ ሆነ ነው። ሰውማ እኮ ቢኖረን ኖሮ፥ ከአባ ጳውሎስና ከግብር አበሮቻቸው የተለየ ሰው ሁለት ሦስት ሰው እንኳ ቢኖር ይሆን ነበር። ሌላ ቀርቶ አባ ጳውሎስ ቢሞቱ አንድ ጳጳስ ለመሾም እነዚህ በዚያ ሕግ ላይ የፈረሙት ጳጳሳት ሁሉ የመሾም መብት ስለሌላቸው፤ በዚያ ሕግ ላይ ያልፈረመ ጳጳስ ሦስት ከሌለ ቤተ ክርስቲያኒቱ እንደገና ፓትርያርክ መሾም አትችልም ይህን ዕወቁ አትችልም። እንደገና ወደ ግብጽ መሄድ ነው።"

በወቅቱ የቀረቡት ጥያቄዎች በርካታ ሲሆኑ፤ እንደ አግባቡ መልስ ተሰጥቶባቸዋል። እኛም እነዚህ ጥየቄዎችና መልሶች አሁን ቤተ ክርስቲያኒቱ ያለችበትን ሁኔታ የሚያመላክቱና መፍትሔ የሚጠቁሙ ሆነው ስላገኛናቸው ለእናንተ ለምእመናን ለማቅረብ ወደድን። በ፲፱፻፺ / ምእመናን በሊቀ ሊቃውንት አለቃ አያሌ ታምሩ መኖሪያ ቤት ተገኝተው በወቅቱ ያቀረቡላቸው ጥያቄዎች፦

፩፦ ውግዘት ማለት ምን ማለት ነው?

፪፦ አንድ ሠው ተወገዘ ሲባል ምን ምን ሲሰራ ነው?

፫፦ በፓትርያሪኩና በእርስ መካከል የተፈጠረው ችግር ለመፍታት ለምን አልተቻለም?

፬፦ ፓትርያ ቢያጠፉ ወይም ሃይማኖት ቢያፋልሱ እራሳቸው በሰሩት ራ ይቀጣሉ እንጂ፤ ካህናት አባቶች ተባባሪዎች ናቸ ተብለው ለምን ይወገዛሉ?

፭፦ ቤተ-ክርስቲያናችን ሁልጊዜ ስለ ፍቅር እያስተማረች፤ በእርዎና በፓትርያሪኩ መካከል ለምን ፍቅር ጠፋ?

፮፦ መኑስ ለምን በቤተ-ክርስቲያን ተገኝቶ እንዳያስቀድስ ታገደ?

፯፦ ሠው በቤተ-ክርስቲያን ተገኝቶ አስቀድሶና ሥጋ ወደሙ ለመቀበል ለምን ተከለከለ?

፰፦ የጌታ ሥጋ ወደሙ በካህናት አባቶች እጅ አትቀበሉ፤ የፓትርያሪኩ ተባባሪዎች ናቸው ለምን ተባለ?

፱፦ የእናንተ የሃይማኖት አባቶች ፍቅር መጥፋት፤ ለመናፍቃን፥ በር አይከፍትም ወይ?

፲፦ ዛሬ ዛሬ መናፍቃን በእነሱ በኩል ፍቅር ጠፍቷል፣ እንደምታቸው አንዱ አንዱን እየወገዘ ነው ያለ” እያሉ ይሳለቁብናል። በእርሶ በኩል ይኼን እንዴት ያዩታል?

፲፩፦ ይኽ ውግዘት የተላለፈው ለመላው ኢትዮጵያ ሕዝብ ነው፤ ወይስ ለአዲስ አበባ ከተማ ብቻ?

፲፪፦ ይኼን ውግዘት የተቀበሉ ቤተ-ክርስቲያኖች ስንት ናቸው፣ በውግዘቱስ አምነውበታል፤ ይኼንንም እንዲያብራሩልን?

፲፫፦ የጌታችን የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ቅዱስ መስቀል በካህን አባቶች እጅ አትሳለሙ ለምን ተባለ?

፲፬፦ ውግዘት ከተላለፈ ወዲህ ብዙ እናት አባቶች፣ ኅት ወንድሞች ከዚህ ዓለም በሞት የተለዩ አሉ፣ እነዚህ ሠዎች፥ እንደተወገዙ ነው የሞቱት ወይስ ተፈተው፤ ይኼንንም እንዲያብራሩልን?

፲፭፦ ይኼ ውግዘት በግል ጋዜጣ ከማስተላለፍዎ በፊት ለምን በየቤተ-ክርስቲያኑ ተገኝተው ለምመኑ አላስተላለፉም?

፲፮፦ ይኽ ውግዘት እስከመቼ ነው የሚቆየው፤ ለምን?

፲፯፦ ይኽ ውግዘት ከአዲስ አበባ ውጭ የሰማ ሃገር አለ? ካለ፥ ውግዘቱን ተቀብሎታል ወይንስ አልተቀበለውም?

፲፰፦ ይኽ ውግዘት ብጹዕ አባታችን ሰምተዋል ወይስ አልሰሙም?

፲፱፦ ብጹዕ አባታችን የግል ጋዜጣ ገዝታችሁ አታንብቡ ብለው አውግዘዋል፣ የእርሶ ውግዘት የተላለፈው ደግሞ በግል ጋዜጣ ነው፤ ይኼ ሊጋጭ አይችልም ወይ?

፳፦ አንዱ ያወገዘው አንዱ ሊፈታው አይችልም ወይ? ካልቻለ፥ እስከመቼ በውግዘት ውስጥ ልንኖር እንችላለን? ወይስ ከቤተ-ክርስቲያን እስከመቼ እርቆ ሳያስቀድሱ ቆያ?


ለቀረበላቸው ሙሉ ጥያቄዎ የሰጡትም እጹብ ድንቅ ምላሻቸውመልሶቻቸ ይስሙ፤ ያዳምጡ።


ለአባታችን ሊቀ ሊቃውንት አለቃ አያሌ ታምሩ፥ ቃለ ሕይወትን ያሠማልን፤ መንግሥተ ሠማያት ያውርስልን፤ ጸጋ ረድኤት በረከታቸው ይደርብን፤ አሜን።
-----------------------------------------------------

No comments:

Post a Comment