Monday, April 6, 2015

ሆሣዕና በአርያምና የካህናት አለቆችና የጻፎች ክስ (ማቴ ፳፩፥፲፭-፲፮)



በስመአብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን።

አንዳንድ "ክርስቲያን ነን" ባዮች፤ እንደ ካህናት አለቆችና ጻፎች ተቆጥተው፦ "ሆሣዕና ምንድን ነው?" የሚሉ፣ እናውቀናለን ብለውም አላዋቂነታቸው የተቆጡበት የኑፋቄ ቃላቸውና ድምጻቸው ያስታውቃል።  የዘመናችን የካህናት አለቆችና ጻፎችም ኧሊህ ናችው! ከአስመሳይነት ውጭ ኢየሱስን እንኳን በምዕሉ በጥቂቱም ኧረ እንደውም እጅግ በጥቂቱ አያውቁትም!

ለዚህም ነው የዛሬዎች የካህናት አለቆችና ጻፎችም፦ «ሆሣዕና ለዳዊት ልጅ እያሉ የሚጮኹትን ልጆች ባዩ ጊዜ፥ ተቆጥተው» "በኦርቶዶክስ እምነት እንዲህና እንደዚህ ታደርጋለች" እያሉ፤ በአምላካችንና በመድኃኒታችን፣ በመድኅነ ዓለም በክርስቶስ ፊት ሊከሱን ያደባሉ፤ ዳሩ ግን መጥምቀ ዮሐንስ እንዲህ ተብሏል፦ «ዳሩ ግን ከፈሪሳውያንና ከሰዱቃውያን ብዙዎች ወደ ጥምቀቱ ሲመጡ ባየ ጊዜ፥ እንዲህ አላቸው፦ እናንተ የእፉኝት ልጆች፥ ከሚመጣው ቍጣ እንድትሸሹ ማን አመለከታችሁ? እንግዲህ ለንስሐ የሚገባ ፍሬ አድርጉ፤ በልባችሁም፥ አብርሃም አባት አለን እንደምትሉ አይምሰላችሁ፤ እላችኋለሁና። ከነዚህ ድንጋዮች ለአብርሃም ልጆች ሊያስነሣለት እግዚአብሔር ይችላል።» (ማቴ ፫፥፯-) ተብሎ የተፃፈውን ከቶ አላነበባችሁምን? በእውኑ ይኼ ድንጋይ ምንድን ነው? ከድንጋይስ፥ ለአብርሃም ልጆች ሊያስነሣለት እግዚአብሔር ይችላል የተባለውስ ምንድን ነው? ደግሞስ የተፈጥሮ ድንጋዮች አመሰገኑት ወይ? ለአብርሃም ልጆች ሊያስነሣለት በድንጋዮች አንፃር የተነገረውስ እነማን ይኾኑ? ከሳሽና ወቃሽ ድሮም ነበሩ፣ አሁንም አሉ፤ ወደፊትም ይኖራሉ! የአብርሃም ልጆች ድንጋዮች ይኾኑ ወይ? ለዚህ ምላሽ መጽሐፍ ቅዱስ ምን ይለናል፦
 
የሕይወት ቃል፣ እውነተኛው የሃይማኖት ምስክራችን መጽሐፍ ቅዱስ እንዲህ ይላል፦ «አንቺ የጽዮን ልጅ ሆይ፥ እጅግ ደስ ይበልሽ፣ አንቺ የኢየሩሳሌም ልጅ ሆይ፥ እልል በዪ፤ እነሆ፥ ንጉሥሽ ጻድቅና አዳኝ ነው ትሑትም ሆኖ በአህያም፣ በአህያይቱ ግልገል በውርጫይቱ ላይ ተቀምጦ ወደ አንቺ ይመጣል። የዘንባባ ዛፍ ዝንጣፊ ይዘው ሊቀበሉት ወጡና። ሆሣዕና፤ በጌታ ስም የሚመጣ የእስራኤል ንጉሥ የተባረከ ነው እያሉ ጮኹ።» (ዘካ ፱፥፱፤ ማቴ ፳፩፥፱-፲፭፤ ማር ፲፥፱-፲፤ ዮሐ ፲፥፲፫)

በሌላ በኩል ደግሞ፥ የካህናት አለቆችና ጻፎች በልበ አምላክ በነቢየ ዳዊት ትንቢት የተተነበየውን የትንቢት ቃል እያነበቡት አልገባቸውም፣ የትንቢቱም ፍጻሜም እንዲህ ተብሎ ተጽፏል፦ «ከሕፃናትና ከሚጠቡ ልጆች አፍ ምስጋናን አዘጋጀህ ስለ ጠላትህ፥ ጠላትንና ቂመኛን ለማጥፋት። አቤቱ፦ እባክህ፥ አሁን አድን፣ አቤቱ፦ እባክህ፥ አሁን አቅና። በእግዚአብሔር ስም የሚመጣ ቡሩክ ነው፤ እግዚአብሔር ቤት መረቅናችሁ።» (መዝ ፰፥፪፤ ፻፲፯፥፳፭-፳፮) ተብሎ ተጽፏል።

        በሆሣዕና ዕለት፥ የካህናት አለቆችና ጻፎችም ክስ፦ እያነበቡ አልተረዱትም፣ "አብርሃም አባት አለን" (የዛሬዎቹ ደግሞ ኢየሱስ ብቻ) ከማለት ውጭ ያነበቡትን ወደ ተግባር ሲደረግ ሲያዩ እየተቆጡ፣ የአምልኮ ኃይል አጡ፣ ለማመን አቃታቸው፣ ለዚህም ነው፥ የተነገረውና የተተነበየው ትንቢቶች ሲፈጸም የተመለከቱት የካህናት አለቆችና ጻፎችም እንዲህ ብለው አጉረመረሙ፦ «ነገር ግን የካህናት አለቆችና ጻፎች ያደረገውን ድንቃ ድንቅ በመቅደስም፤ ሆሣዕና ለዳዊት ልጅ እያሉ የሚጮኹትን ልጆች ባዩ ጊዜ፥ ተቈጥተው እነዚህ የሚሉትን አትሰማምን? አሉት። ኢየሱስም እሰማለሁ፤ ከሕፃናትና ከሚጠቡት አፍ ምስጋናን ለራስህ አዘጋጀህ የሚለውን ቃል ከቶ አላነበባችሁምን? አላቸው።» (ማቴ ፳፩፥፲፭-፲፮) በእርግጥም "ክርስቲያን ነን" ባዮች እንደ ካህናት አለቆችና ጻፎች ተቆጥተው፦ "ሆሣዕና ምንድን ነው?" ብለው ሲጠይቁ፤ አንብበናል ቢሉም ዳሩ ግን በነቢያትና በመዝሙራት፣ በትንቢትና በወንጌል የተጻፈውን ከቶ አላነበባችሁምን? እንላቸዋለን።




«ሆሣዕና በአርያም» ክብርና ምስጋና ድንግል ልጅ ኢየሱስ ክርስቶስ ይኹን! አሜን። (ማቴ ፩፥፳፫፤ ፳፩፥፱)

Friday, April 3, 2015

ክብር መስጠት፤ ቀሲስ ሰሎሞን ሙሉጌታ


                               በስመአብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን።

ሰዎችን ማክበር ትኩረታቸውን ለማግኘት ይረዳናል። እግዚአብሔርን የምናምንና ስላመነውም ምስክርነት የምንሰጥ ሰዎች ሁሉ ሁሉን ማክበር ይጠበቅብናል። ሽማግሌም ሆነ ወጣት፣ የታመመ ሆነ ጤነኛ፤ ድሃም ሆነ ባለጠጋ፤ የተማረም ሆነ ያልተማረ፤ ወንድም ሆነ ሴት፤ ጻድቅም ሆነ ኃጥእ ሁሉን ማክበር ይጠበቅብናል፡፡ እነዚህ ሰዎች አስቀድሞ የነበራቸው ልምድ ምንም ይሁን ምን፣ አመለካከታቸውና ሥነ ምግባራቸውም መልካምም ይሁን መጥፎ እንድናከብራቸው ይጠበቅብናል።

ሰዎችን የምናከብራቸው በተለያዩ ምክንያቶች ነው፤ በቅድሚያ እግዚአብሔር በአምሳሉና በአርአያው ስለ ፈጠራቸው እናከብራቸዋለን። ስናከብራቸውም ያከበርነው የተፈጠሩበትን የእግዚአብሔርን አምሳልና አርአያ መሆኑን ማወቅ ይጠበቅብናል። ሰዎችን የምናከብርበት ሁለተኛው ምክንያት እግዚአብሔር ልጁን ለሰው ዘር ሁሉ መሥዋዕት ይሆን ዘንድ ስለሰጠ ነው። ይህን የማዳን ሥራ እግዚአብሔር ከፈጸመላቸው ታላቅ መሥዋዕትነትም ከከፈለላቸው ታዲያ ቢያንስ ይህ የተደረገላቸውን ሰዎች ማክበር አይጠበቅብንም ይሆን? ሦስተኛው ሰው ምንም ያህል ክፋት ወይም መጥፎነት ቢኖርበትም በውስጡ ግን መልካምነት ስለሚገኝበት ሰውን ልናከብረው ይገባል።

ሰውን ማክበር በውስጣችን የሚገኘውን መልካምነት መቀስቀሻ መሣሪያ ነው፤ ይህም ሰው ክርክርንና ራሱን መከላከልን ትቶ ለነገሮች ጆሮ ሰጥቶ ለመስማት ያበቃዋል። ማክበር ሰውን ሳናስገድድና ሳናስጨንቅ ለመስማት የሚችልበት ነጻነት እንድንሰጠውና በእግዚአብሔር ጸጋ በመታመን ወደ ምሥራቹ ወንጌል ለመጥራት ይረዳናል፤ ጥሪያችንን ካስተላለፍን በኋላ የምሥራቹን ወንጌል መቀበልም ሆነ አለመቀበል ግን የእያንዳንዱ ሰው ፈንታ ነው።

ክብር መስጠት ስንል የሰው የግል መብቱን ነፃነቱንና ምስጢሩንም ማክበርንም ያካትታል፤ ስለዚህ ምንም በቅርበት የምናውቃቸው እንኳ ብንሆን ሰዎችን ወደ ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ሃይማኖታችን ለማቅረብ የምናደርገው ጥረት የሚሳካው በግኑኝነታችን ወይም በንግግራችን ወቅት ክብር ሰጥተን በምንጓዘው መንገድ ርቀት ነው። ክብር መስጠት የሰውን ስሜት የሚጎዱ ቃላቶችን አለመጠቀምን ያካትታል። የሰዎችን ባሕል፣ እሴቶቻቸውን፣ የቀደመ ታሪካቸውን በአግባብ መረዳትና ማወቅ ክብራቸውን የሚጎዳ ስህተት ከመሥራት ይታደገናል። ይህም ማስተዋል የተሞላበት አካሄድ እግዚአብሔር በመንገዱ እንዲመራን ለመጠየቅና ለመጸለይ ይረዳናል፤ ምንም ብናውቅ ሰውን ሊያስቀይሙ አጋጣሚዎች ሊፈጠሩ ይችላሉና።

Friday, March 13, 2015

እንደገና ወደ ግብጽ መኼድ፦ ሊቀ ሊቃውንት አለቃ አያሌው ታምሩ



በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አመራር ላይ ከቅርብ ዓመታት ወዲህ በተደጋጋሚ የተከሰቱትን የሃይማኖት ትምህርትና የሥርዓት መበላሸት በማስመልከት የቤተ ክርስቲያኒቱ የሊቃውንት ጉባኤ ሰብሳቢ የነበሩት አለቃ አያሌው ታምሩ ችግሩ ሥር ሳይሰድ ገና ከጅምሩ እንዲታረም ማሳሰቢያና ተማጽኖ ለቤተ ክርስቲያኒቱ ቅዱስ ሲኖዶስ ተደጋጋሚ ተማጽኖ አቅርበው ነበር። ነገር ግን ጥያቄአቸው በቅዱስ ሲኖዶስ ዘንድ በቸልታ በመታየቱ ምክንያት፤ አለቃ አያሌው ታምሩ ባላቸው ከፍተኛ ሥልጣንና ኃላፊነት፤ በቤተ ክርስቲያን ላይ ዐመጽ የሚፈጽሙትን ፓትርያርኩንና ተከታዮቻቸውን ማውገዛቸው ይታወቃል። ቃለ ግዝታቸው በመጀመሪያ የወጣው ሰኔ ፳፯ ቀን ፲፱፻፹፰ / «መብሩክ» ጋዜጣ ላይ ነበር። ሙሉውን ቃለ ውግዘት ለማንበብ ከዚህ ይጫኑ

አባታችን ይህን ቃለ ውግዘት ካስተላለፉበት ጊዜ ጀምሮ፤ ከምእመናንና ከተለያዩ ክፍሎች ውግዘቱን አስመልክቶ የተለያዩ ጥያቄዎች በቃልና በጽሑፍ፥፣ እንዲሁም በተለያዩ ጋዜጦች ላይ የቀረቡላቸው ሲሆን፤ ለቀረቡት ጥያቄዎችም ተገቢ የሆኑ ምላሾችን ሰጥተዋል ሰጥተዋል። በተለያዩ ጊዜዎች ከቀረቡላቸው ጥያቄዎች መካከል በ፲፱፻፺ / ብዙ ምእመናን በመኖሪያ ቤታቸው ተገኝተው በጋራ ያቀረቡላቸው ሲሆን፤ ከእነዚህ ጥያቄዎች መካከል አንዱ "በዚህ ውግዘት መካከል በእርስዎ ወይም በሳቸው መካከል የመለየት ባሕርይ ቢኖር ውግዘቱ እንደ ታሰረ ነው ወይስ እንደ ተፈታ ነው የሚቆየው? ውግዘቱን ማን ይፈታዋል? እስከ መቼ ድረስ ነው ውግዘቱ የሚቆየው?" የሚል ሲሆን፤ ክቡር አባታችን የሚከተለውን ምላሽ ሰጥተው ነበር።