Friday, May 9, 2014

ልዩ ናት!

ሰይጣን፥ በፈጣሪ መኖር ያምናል፤
ስቶ፥ ለማሳሳትም ቡዙ ይደክማል፤
ከቅዱስ ቃሉም፥ ጥቅስ ይጠቅሳል፤
ቅሉ፥ ይጐለዋል የሃይማኖት ኃይል።

እኔ ሰይጣንን እንዴት ልምሰለው፤
በኤልሻዳይ፥ መኖር የማምነው።

ቅዱሳኑን፥ ለማጥላላት፣ ያለ አግባብ ቃሉን መወርውር፤
ከአምላኬ ነጥዬ፣ እናቱን ላለመቀበል ኅሊናን ማስነውር፤
ላልተገባ ነገር፥ ጥቅስ መጠቃቀስ፣ ብዙ ጊዜ መዳከር፤
ሰይጣን፥ ይለየኛል ከሕይወት ቃሉ፣ ከክርስቶስ ፍቅር።
 
ዲያብሎስ፥ ይጎለዋል፣ የሃይማኖት እምነት፤
ለምን? ልምሰለው፥ ከእርሱ ጋር በሕብረት።

ሰይጣን፥ ቃሉን ያውቃል ኃይሉን ይክዳል፤
እንደተባለው፥ እጅግም ይንቀጠቃጥማል፤
ያኔ ክርስቶስ የዳዊት ልጅ ተብሎ ተነግሯል፤
ዛሬማ፥ ይኼ እጹብ ድንቅ ቃል ይናፍቀናል።

ዓይኑ እንዲያይ የዳዊት ልጅ ብሎ፤
የአባቶቹን ፈለገ-መንገድ ተከትሎ።

ሕያው ቃሉ፥ ማርያም እናቱ እንደኾነች፤
ያስረዳናል፥ በአምላክ እንደተመረጠች፤
ልዩ ናት! ድንግል እናታችን ለምስራች፤
ከመልአኩ ገብርኤል ሥሙን የሰማች።

እናንተ ሰይጣናት ከእኔ ተፋቱኝ፤
ስለ እናቱ ልዕልና መስካሪ ነኝ።

እኔስ የምለየው፥ ከሰይጣን ምስክርና ማህበር፤
የዳዊት ልጅ፣ የድንግል ልጅ ስል ነው በፍቅር፤
ቃሉ ያስገድደኛል፥ ስለ ቅዱሳኑ እንድመሰክር፤
እንዲከብሩ እርሱ ለመረጣቸው እግዚአብሔር።

ከሕይወት ምንጭ፥ በቃሉ ነፍሴ እንዲኖር፤
እመስክራለሁ፥ በሕያው ጥላ ሳልጠራጠር።

እስኪ ንገሩኝ፥ ጥፋቴ ምኑ ላይ ነው?
ምንድን ነው ኃጢያቴ? እኔስ እላለው፤
የድንግል ልጅ ኢየሱስ፥ በሥጋ የተወለደው፤
ክርስቶስ፥ የተዋሕደው በቀረልን ዘር ነው።

<<ወስብሐት ለእግዚአብሔር ወድንግል ማርያም ክብር፤ አሜን>>
(//፳፻፮ /)

No comments:

Post a Comment