Sunday, June 1, 2014

"ጠንቋይና አስጠንቋይ" በመልአከ ሰላም ቀሲስ ደጀኔ ሺፈራው


,,, እንዲህ የሚያስጨክን፥ የማይገባ ሥራ የሚያሰራ ሰይጣን ነው። በየ-አንዳንዱ ጎጆ (መኖርያ ቤት) ውስጥ ቢገባ ብዙ ጉድ አለ! ተስፋውን በጥንቆላ ላይ አድርጎ የሚኖር፣ ጠንቋዩ፥ በመከረው ምክር የሚመላለስ፣ ያንን በይፈጽም እንደው ዕለቱን መሬት-ተከፍታ የምትውጠው የሚመስለው አለ። በጥንቆላ፣ በመተት፣ በአስማት፤ ወገኖቻቸውን የሚያሳብዱ፣ ወገኖቻቸውን የሚገድሉ፣ ወገኖቻቸውን የሚያፈዙ፤ ጥቂት አይደሉም።

እገሌ እኮ የዩኒቨርስቲ ተማሪ ነበረ፤ አሁን ግን ጨርቁን ጥሎ የሚኼደው። ምን ነካው? "ጓደኛው ነው ያቀመሰው አሉ" ይባላል። እገሌ እኮ ጥሩ ደሞዝ ነበረ፣ እንዲህ ዐይነት ቦታ ይሠራ ነበር፤ አሁን እንዲህ ከንቱ ኾኖ ቀረ። ምን ኾነ? "ጓደኛው ነው እንዲህ ያደረገው" ይባላል። እገሌ እኮ እንዴት ያለ ነጋዴ ነበረ፣ ቢጠሩት የማይሰማ፤ አሁን ግን ከንቱ ኾኖ ቀረ። ምን ኾነ ታዲያ? "አይ፥ በንግዱ የቀኑበት ሠዎች ናቸው እንዲህ ያደረጉበት" ይኼንን ነው የምንሰማው።

በአካባቢው፥ በመንደሩ፤ የሚነገረው ይኼ ነው። ጠንቋይ፥ ቤት የሚያድረው ሕዝብ፣ ቃልቻ፥ ቤት የሚያድረው ሕዝብ፤ ብዛቱ፥ ቁጥር-ስፍር የለውም። ምንድነ ነው የሚሻለን ታዲያ? የእግዚአብሔርን ቃል፥ አልሰማንም እንዳንል፤ ሰምተናል! ተአምራቱን፥ አላየንም እንዳንል ዐይተናል! ግን ሰምተን እንዳልሰማን ኾንን፣ ዐይተን እንዳላየን ኾንን! የአንዳችንም ሕይወት ሲለወጥ ዐይታይም።

ተማሪው፥ "ትምህርት እምቢ አለኝ" ሲል፤ እንደው፦ "ጠንቋይ ቤት ሂድ ጠንቋዩ ይነግርሃል፤ እቃልቻው ቤት ብትሄድ ይነግርሃል" ይባላል፤ እውነት መስሎት ይሄዳል። ነጋዴውም፥ "ንግድ እምቢ አለኝ ምን ማድረግ ይሻለኛል" ሲል፤ "እጠንቋዩ ጋር ብትሄድ፤ እቃልቻው ቤት ብትሄድ" ይባላል። መሪ፥ መካሪ አለው እርሱም (ርኩስ የሰይጣኑን መንፈስ) ሥራ፥ ፈልጌ፣ ፈልጌ አጣኹ፤ ምን ይሻለኛል? ሲል፤ "እጠንቋዩ ጋር ብትሄድ፣ እቃልቻው ቤት ብትሄድ፤ ሥራ ታገኛለህ" ይኼ ደካማ ሕዝብ ሥጋዊ ፍላጎቱን ለሟሟላት ሲል፥ ሃይማኖቱን ሽጦ፣ ለውጦ፤ ከአምልኮተ እግዚአብሔር ሲንሸራተት፣ ሲያፈገፍግ ይታያል።

እንደው፥ ዘመኑ ዓመተ ምዕረት ኾኖ፤ እግዚአብሔር፥ ኃጢያት፣ በደላችንን ሸፍኖልን ነው እንጂ! የእየ-አንዳንዳችን ኃጢያት በየግንባራችን የሚፃፍ፣ የሚገለጥ ቢኾን ኖሮ ከእኔ ጀምሮ ኹላችንንም ብንኾን ከዚህ ቦታ ባልተገኘንም ነበር! እንደውም፥ ጥንቆላ የተስፋፋበት ዘመን ነው። በየ-ጋዜጦች ላይ የምናነበው፤ ጥንቆላ አይደለ? ወይስ የእግዚአብሔር ነቢያት ነው የፃፉልን? ትንቢተ ማን እንበለው? ግራ-የሚገባ (የሚያጭበረብር) ነገር እኮ ነው።

"በሚቀጥለው ሳምንት፥ እንደዚህ ታሳልፋለህ፣ ይኼን ታገኛለ፣ ይኼን ታጣለህ፣ እንዲህ ዐይነት ቦታ ብትሄድ ጥሩ ነው፤ እንደህ ዐይነት ቦታ ባትሄድ ጥሩ ነው" ይላል። በእዚህ ልቡ ያልተሰለበ የለም ዛሬ! የቤተ-ክርስቲያን ልጆች ነን! ከምንል ጀምሮ፥ በእዚህ ያልተሰነካከልን የለንም! "የእኔ ኮከብ የትኛው ነው?" ብለን ካጠናን በኋላ፤ የምንከታተል ሠዎች አለን። ሰይጣን ሳናውቀው እያጠመደን ነው ማለት ነው። በእዚህ የተነሳ፥ ሕይወታቸው የተበላሸባቸው፣ ያቀዱትን ዕቅድ ያፈረሱ፣ ትዳራቸውን ደግሞ ችላ ያሉ ሠዎች አሉ።

"እንዲህ ዐይነት ኮከብ ያላት ሴት አጥፊህ ናት" ይላል "እንዲህ ዐይነት ኮከብ ያለው ወንድ አጥፊሽ ነው" ሃሃ,,, የሚስቴ ኮከብ እኮ ይኼ ራሱ ኮከብ ነው፣ የባሌ ኮከብ ራሱ ይኼ ራሱ ኮከብ ነው፣ በእዚህ ወር ነው የተወለደው፤ ተመልከቱ! ሰይጣን በጸና ትዳር መካከል ሲገባ፣ በጓደኛም መካከል፥ "እንዲህ ዐይነት ኮከብ ያለው ሠው አትፊህ ነው" ከተባለ፤ እስኪ፦ "የጓደኛዬ ኮከብ፥ በምን ወር ነው የተወለደው ልየው" ይባላል። ሲያየውም፥ እንደራሱ አድርጎ የሚያየውና የሚወደውን ጓደኛውን መጠርጠር ይጀምራል፣ ገሸሽ ማድረግ ይጀምራል፤ ከእዚህ ነፃ የኾነ ሠው ማነው? እየ-አንዳንዳችን "እኔ ማን ነኝ?" ልንል ያስፈልጋል።

*,,, የጠንቋዮችን ምትአት፣ የሰይጣንን ስራ በሙሴ በትር ያጠፋ ማነው? እግዚአብሔር ነው! ዛሬም፥ መተት ቢመተት፣ ድግምት ቢደገም፣ የተለያየ ምትአት ቢሰራ፣ በምልክት ሕዝቡን ለማጥፋት ቢጥሩ፣ በአባቶቻችን መስቀል ይኼ ሁሉ ይጠፋል? አይጠፋም? ይጠፋል! ምን ግን ያስፈልጋል ለእዚህ? ፍጹም እምነት! ፍጹም እምነት ያስፈልጋል!

*መስቀል ሰይጣን አይወድም! ለምን? ምትአቱ ቢሰራ፥ በመስቀሉ፥ ምትአቱ ይጠፋል? አይጠፋም? ይጠፋል! ስለዚህ አይወድም። መስቀሉን የሚጠሉ መናፍቃንን ያስነሳ ማነ ነው? ሰይጣን ነው! ለምን እንጨት እንሳለማለን በሉ እያላቸው ሹክ እያላቸው! ግን እውነት እንነገገር! እውነት እንነገገር፥ ሰይጣን የለከፈው ሠው፥ መስቀሉ ግንባሩ ላይ ሲቀመጥ ዝም ይላል? ዝም ይላል ወይ? ምንድን ነው የሚለው? ይጮሃል፣ ይለፈልፋል! ኹለተኛ እዚህ ሥፍራ (ሠውነት ላይ) አልደርስም ይላል! ሰይጣን መስቀልን ይሸሻል።

*አንዳንድ መናፍቃን፥ አባቶቻችን ሳያውቁ እንዲህ መስቀል ሊያሳልሟቸው ሲሉ ይሸሻሉ። በውስጣቸው ያለ ማነው? የክርስቶስ የኾነ መስቀልን ይጠላል? የዳነበትን ይጠላል? አይጠላም! ተመልከቱ እኛ፥ እምነት ብቻ ይኑረን እንጂ! እመስቀሉን ስንሳለም እርሱ (ርኩስ የሰይጣኑን መንፈስ) ይሸሻል! አይሸሽም? ይሸሻል! አይቀርበንም፤ ተቃጠልኹ፥ ተቃጠልኹ ነው የሚለው!

*በሙሴን በትር፦ የፈርኦ ጠንቋዮችን፥ መተቱን፣ ምትአቱን ያጠፋል አምላክ፤ ዛሬም፥ መተቱን፣ ምትአቱን ያጠፋል። አንዳንድ ጠንቋዮች፣ መተተኞች፣ ቃልቾች፤ እንደዚህ ዓይነት ትምህርት ሲሰጥ አይወዱም! አይወዱም! ቆይ፥ ባልሰራለት ይላሉ! እኔ፥ እርሱን ባላሳብደው፣ ባልገድለው የለውም ይላሉ! ይፎክራሉ!(ከድምጽ ወ መንፈሳዊ  ትምህርታቸው ወደ ጹሑፍ ተቀንጭቦ የቀረበ)
----------------------------------------------------- /// ----------------------------------

ጠንቋይና አስጠንቋይ ማለት ምን ማለት ነው? (ከወዳጆቼ፥ ልክ የቀረበልኝ)

ጠንቋይ ማለት፦ ኅሊናውን፣ ልቦናውን፣ አዕምሮውን፣ ስብህናውን፣ አጠቃላይ ማንነቱን፤ ለእርኩስ መንፈስ ለሰይጣን ያስገዛ ነው። ራሱን ለዚህ የሰይጣን መንፈስ ሲያስገዛ፦ እርኩስ መንፈሱ የሚገልጥለትን፣ የሚያሳየውን፣ ሹክ የሚለውን፣ በምዕናብ የሚመለከተውን፤ በመናገርና በማድረግ፣ በሰይጣን መንፈስ እየተመራ፣ የሚጠንቁል ማለት ነው።

አስጠንቋይ ማለት ደግሞ፥ በትንሹ ስለ አራት ምክንያቶች እንመልከት፦

፩ኛ፤ አስጠንቋይ ማለት ከሰይጣን መንፈስ እርዳታን ፈልጎ ወደ ጠንቋዩ የሚኼዱ፣ ክፉ መንፈስን በመጠጋት፦ ለራስ፥ ለሃብት፣ ለውበት፣ ለግርማ-ሞገስና ሌሎችም ,,,,,,,ተ።

፪ኛ፤ ሠውን ለመጉዳት ደግሞ በሰዎች ስቃይ ለመደሰት፣ በትምህርትና በእውቀት የማይወዷቸውን ለማፍዘዝና በድንግዝግዝ ሕይወት ውስጥ እንዲኖሩ ለማድረግ።

፫ኛ፤ በመንፈሳዊ ሕይወት ውስጥ ያሉትን ደግሞ በፍቅረ ንዋይ፣ በፍቅረ ሲመት፣ በኃጢአት የመቃጠል ስሜት፣ በዝሙት፣ በርኵሰትና በክፉ ምኞት፣ ስለ በጎቹ ግድ እንዳይላቸው፤ በማድረግ እረኛውን መጠቋቀሚያ፣ በጎቹን ደግሞ፥ በእረኛቸው መሰነካከል ምክንያት፣ ቅጥ ያጣ ስግብግብነት እንዲያድርባቸው ለማድረግ፣ በፍትወት፣ የዓለምን ምኞት እንዲወዱ ማድረግ፣ ተስፋ እንዲቆርጡና እንዲቅበዘበዙ፣ ሥጋዊ ወመንፈሳዊ ሕይወት እንዲያስጠላቸው ማድረግ።

፬ኛ፤ ሰራተኛውን ደግሞ በስራው ደስተኛ እንዳይኾን ለማድረግ፣ በፍቅረኞችና በባለ-ትዳሮች መሐል፥ ሠላምና ፍቅር አጥተው እንዲባሉና እንዲነታረኩ እንዲኹም እንዲለያዩ፥ ልጆች ያለ እናትና አባት ፍቅር እዲያድጉ ለማድረግ፣ ለሚወዳትና ለሚያፈቅራት ወይንም ለምትወደውና ለምታፈቅረው ሠው፥ በሰይጣኑ መንፈሱ በመስተፋቅር ኃይል ለራስ ለማድረግና ሌሎች ,,,,,,, በርካታ ነገሮችን በመሻት፤ የእርኩሱን የሰይጣኑን መንፈስ በመፈለግ የሚኳትኑ፣ የጠንቋዩን ደጅ የሚጤኑ፤ ማለት ናቸው።

(ለዚህና ለመሰል ጥያቄያችን ሁሉ እግዚአብሔር መልስ አለው እንዳለው በማመላከትና እውነተኛውን የመልአከ ሰላም ቀሲስ ደጀኔ ሺፈራው፥ አስተምሮታቸውን ለበለጠ ለመረዳት፥ መንፈሳዊ ትምህርታቸውን እንዲያዳምጡ ፈሳ ግብዣዬና ምክሬን እለግሶታለሁ። እግዚአብሔር አምላክ፦ ለአባታችን መልአከ ሰላም ቀሲስ ደጀኔ ሺፈራው፥ ቃለ ሕይወት ያሰማልን፤ መንግሥተ ሠማያት ያውርስልን! እያልኹኝ፥ እኛም ሰምተንና አዳምጠን፥ አንድም ሠላሳ፣ ስልሳ፣ መቶ፤ ፍሬ እንድናፈራ የእግዚአብሔር ፍቃድ ይሁንልን! ወስብሐት ለእግዚአብሔር ወድንግል ማርያም ክብር!!! አሜን።

No comments:

Post a Comment