Tuesday, June 18, 2013

መጽሐፍ ቅዱስ ስለ መድኃኒታችን ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ ብቻ ነው የሚናገረውን?


        ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ በተለያየ መልክቶቹ "ነገር ግን ዓለም ለእኔ የተሰቀለበት እኔም ለዓለም የተሰቀልሁበት ከጌታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ መስቀል በቀር ሌላ ትምክህት ከእኔ ይራቅ።" /ገላ 614/ ቢል "ነገር ግን እኛ ብንሆን ወይም ከሰማይ መልአክ፥ ከሰበክንላችሁ ወንጌል የሚለይ ወንጌልን ቢሰብክላችሁ፥ የተረገመ ይሁን።" /ገላ 18/ ቢለን እንኳን በአንድም በሌላም መንገድ ስለቅዱሳን ይሁንም ስለ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ሳይነግረን፣ ሳያስተምረን፣ ሳይሰብከን፤ ግን አላለፈም።

        ለዚህ ደግሞ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ለቆሮንጦስ ክርስቲያኖች ባስረዳቸው እውነተኛ አስተምህሮ ድንግል ማርያም ንጽሕት፣ ድንግል መሆኗን፤ መስክሯል። ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስም ለክርስቶስ አገልግሎት በተጠራበት ግዜ "እንደ ንጽሕት ድንግል እናንተን ለክርስቶስ ላቀርብ ለአንድ ወንድ አጭቻችኋለሁና" /2ኛ ቆሮ 11 2/ ይላል። ታዲያ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ በትንቢተ ሕዝቅኤል /44 2/ የተነገረውን የእግዚአብሔር ቃል ደግሞ ሲናገር እመቤታችን ድንግል ማርያም ንጽሕት፣ ድንግል፣ ለክርስቶስ በክርስቶስ እንደሆነች አስረግጦ አስረድቶናል።


          ሌላው ደግሞ ስለ እውነትና በእውነት እንዲህ ብሎ ነው የላክላቸው "እንግዲህ ምን እላለሁ? ስለ ጌዴዎንና ስለ ባርቅ ስለ ሶምሶንም ስለ ዮፍታሔም ስለ ዳዊትና ሳሙኤልም ስለ ነቢያትም እንዳልተርክ ጊዜ ያጥርብኛልና።" /ዕብ 1113/ በእውነት ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ በወቅቱ ሐዋርያቶች እንደ ልብ ለመምክር፣ ለመገሰጽ፣ ለማስተማር፤ በማይችሉበት በነበረው ጊዜ እንኳን ውክቢያና እንግልት ግርፋትና ወደ ሞት እልፈት እየተቃረቡ ይህ አስደናቂ ቃል የነቢያቶችን የሐዋርያቶችን ተጋድሎ በሃይማኖት የጸኑትን አባቶችን እንድንዘክራቸው አስረግጦ ነው የሚያስረዳን። ይህንንም ከላይ ሐዋርያ ቅዱስ ጳውሎስ በዕብራውያን ክታቡ በምዕራፍ 11 1-40 በሙሉ ተጋድሎዋቸውን ከገለጸና ከተረከ በኋላ ነው ስለ ሁሉ እንዳልተርክ ጊዜ ያጥርብኛል ያለው።


        ለማንኛውም እንደ እግዚአብሔር ቃል መሰረት ለዕብራውያን ክርስቲያኖች በላከላቸው ክታቡ "እነርሱ በእምነት መንግሥታትን ድል ነሡ፥ ጽድቅን አደረጉ፥ የተሰጠውን የተስፋ ቃል አገኙ፥ የአንበሶችን አፍ ዘጉ፥ የእሳትን ኃይል አጠፉ፥ ከሰይፍ ስለት አመለጡ፥ ከድካማቸው በረቱ፥ በጦርነት ኃይለኞች ሆኑ፥ የባዕድ ጭፍሮችን አባረሩ። ሴቶች ሙታናቸውን በትንሣኤ ተቀበሉ፤ ሌሎችም መዳንን ሳይቀበሉ የሚበልጠውን ትንሣኤ እንዲያገኙ እስከ ሞት ድረስ ተደበደቡ፤ ሌሎችም መዘበቻ በመሆንና በመገረፍ ከዚህም በላይ በእስራትና በወኅኒ ተፈተኑ፤ በድንጋይ ተወግረው ሞቱ፥ ተፈተኑ፥ በመጋዝ ተሰነጠቁ፥ በሰይፍ ተገድለው ሞቱ፥ ሁሉን እያጡ መከራን እየተቀበሉ እየተጨነቁ የበግና የፍየል ሌጦ ለብሰው ዞሩ፤ ዓለም አልተገባቸውምና በምድረ በዳና በተራራ፥ በዋሻና በምድር ጕድጓድ ተቅበዘበዙ።" /ዕብ 11 33-38/ እያለ ስለቅዱሳ አበው ልብን በሚማርክና በሚመስጥ፣ የመንፈሳዊ ጽናታቸውንና ገድላቸውን ይተርክልናል። እዚህ ጋር ከቅዱስ ጳውሎስ ስለ ቅዱሳን አበው መማር፣ ማስተማር፣ ለመድን እንጂ!!!

        
ታዲያ አባቶቻችንና ወንድሞቻችን የሐዋርያ ቅዱስ ጳውሎስን ቃል አብነት አድርገው ስለ ጌዴዎንና ስለ ባርቅ፣ ስለ ሶምሶንም ስለ ዮፍታሔም፣ ስለ ዳዊትና ስለ ሳሙኤልም፣ ስለ ነቢያትና ስሌሎች ቅዱሳን አባቶች እንዲሁም ቅዱሳት እንስት ሲነግሩን ሲያስተምሩን ሲመሰክሩን ለምን ይሆን የሚነቅፏቸው!

        
ሐዋርያው ቅዱስ ሉቃስም አረጋዊው ቅዱስን ስምዖን እመቤታችንን ቅድስት ድንግል ማርያም መባረኩ እንዲህ ሲል ገፆልናል! "ስምዖንም ባረካቸው እናቱን ማርያምን" /ሉቃ 2 34/ በማስከተልም ደግሞ ስለ ቅድስት ሐና በቅድስናዋ፣ በጾም፣ በጸሎት፤ በእግዚአብሔር መቅደስ በሌሊትና ቀን እያገለገለች አትለይም ነበር ብሎ አስተምሮና። /ሉቃ 2 36-37/ ስለዚህም ነው አባቶቻችንና ወንድሞቻችን "የድንግል ማህጸን ፍሬ ክርስቶስ በቤተክርስቲያን ተሞሸረ፣ የክርስቶስ ምእመናን ከቤተክርስቲያን ተጸነሱ። ክርስቶስም፥ ለመታረድ የማያቋርጥ፣ እርዱ የማያልቅ ንጹሕ ላህም፣ በግ ነው። ቅድስት ድንግል ማርያም ከርኩሰትም ሁሉ ንጽሕት፣ ከኃጢአትም ሁሉ የጸራች እንደሆነች የማያምን እርጉም ነው። ሰይጣን በድንግል ማርያም ታመመ፣ በልጇ ተጨነቀ፣ በልጇ መስቀል ስቃይ አገኘው። ስለዚህም ከፍጡራን ወገኖች ሁሉ ሰይጣን ቅድስት ማርያምን ይጠላል።" /ጻዲቅ አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ፥ መጽሐፈ አርጋኖን/

        በሃይማኖት አባቶቻችን ዘንድ "ፊቱ በጨለማ የተሸፈነ ዲያብሎስ በልደት ሥልጣን ያለውን ወልደ እግዚአብሔር ኢየሱስ ክርስቶስ ከድንግል ማርያም ሥጋን ተዋሕዶ ወደ ሲኦል ወርዶ ባየው ጊዜ ፈራ፥ ደነገጠ።" ይሉናል። ግን ለመሆኑ ይህን ከየት አመጡት ተብለው ቢጠይቁ የሐዋርቱን የቅዱሳን ነቢያትቱ ትምህርት በሚገባ ስለተረዱት ስለ ቅዱሳት እንስት እና ስለ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም የሚያስተምሩን በሚገባ እንደተረዱት ያስገነዝቡናል። /ሕዝ 28 13-18 1 ጴጥ 319 ሃይማኖተ አበው ምዕ 2 8/

        
አሁንም ወዳጆች ሆይ፦ ስለ ጌዴዎንና ስለ ባርቅ ስለ ሶምሶንም ስለ ዮፍታሔም ስለ ዳዊትና ስለ ሳሙኤልም ስለ ነቢያትና ስሌሎች ቅዱሳን አባቶች እንዲሁም ቅዱሳት እንስት እንደ እግዚአብሔር ቃል መሰረት እግዚአብሔርን በመፍራት፣ አገልጋዮቹን በማክበር፤ ስለ ሁሉ እንዳልተርክ ጊዜ ያጥርብኛል ይባላል እንጂ! አይ እነዚህን መተረክና ማስተማር ጊዜ ማባከን ነው የሚሉ ካሉ ከሁሉ የከፋ የስህተት ስህተት ነው።

ስብሐት ለእግዚአብሐር!!!

No comments:

Post a Comment