Sunday, January 20, 2013

ስለ ቅዱሳን አበው አጥንት /አፅም/ ስናወራ ይህን እናስብ!

ስለ ቅዱሳን አበው አጥንት /አፅም/ ስናወራ በሁለት መንገድ እንመልከት፦ ይኸውም አንደኛው የግያዝ ዓይኖች (በዚህ ዓይን መንፈሳዊውን ነገር ለመረዳት ስለሚከብድ ባናይበትና ባንመለከትበት እመርጣለሁ) ይህ የግያዝ ዓይን ስጋዊ ደማዊ ብቻ ነው የሚመለከተውና።

ሁለተኛው ደግሞ የኤልሳዕ ዓይኖች፥ ክርስቲያን እንደ መሆናችን መጠን በኤልሳዕ ዓይኖች ስናይ የራቀው ቀርቦ የተሰወረው ተገልጦ በእዝነ ህሊና በዓይናችን ስናይ እንደ እግዚአብሔር ፍቃድና አሳብ የተጋደሉ የቅዱ አበው አጥንት /አጽም/ መጽሐፍ ቅዱስ የሚለንን ዘጠኝ የሚያህሉ እውነታዎችን በደንብ እንረዳበታለን! ይኽውም፦
        1. እግዚአብሔር አምላክም አዳምን ከፈጠረ በኋላ የአጥንት እውነታ፦ እግዚአብሔር አምላክም ከአዳም የወሰዳትን አጥንት ሴት አድርጎ ሠራት ወደ አዳምም እንዳመጣት። አዳምም፦ ይህች አጥንት ከአጥንቴ ናት፥ ሥጋም ከሥጋዬ ናት እርስዋ ከወንድ ተገኝታለችና ሴት ትባል። እንዳለ! /ዘፍ 222-23/

2. ያዕቆብም ልጆቹን ጠርቶ ያዘዛቸው ኑዛዜ ስለ አጥንቱ እውነታ፦ ያዕቆብም ልጆቹን ጠርቶ እያንዳንዳቸውን እንደ በረከታቸው ከባረካቸው በኋላ እንዲህ አላቸው፦ እንዲህ ብሎም አዘዛቸው። እኔ ወደ ወገኖቼ እሰበሰባለሁ በኬጢያዊ በኤፍሮን እርሻ ላይ ባለችው ዋሻ ከአባቶቼ ጋር ቅበሩኝ እርስዋም በከነዓን ምድር በመምሬ ፊት ያለች፥ አብርሃም ለመቃብር ርስት ከኬጢያዊ ከኤፍሮን ከእርሻው ጋር የገዛት፥ ባለ ድርብ ክፍል ዋሻ ናት። አብርሃምና ሚስቱ ሣራ ከዚያ ተቀበሩ ይስሐቅና ሚስቱ ርብቃ ከዚያ ተቀበሩ ከዚያም እኔ ልያን ቀበርኋት እርሻውና በእርስዋ ላይ ያለችው ዋሻ ከኬጢ ልጆች የተገዙ ናቸው። ያዕቆብም ትእዛዙን ለልጆቹ ተናግሮ በፈጸመ ጊዜ እግሮቹን በአልጋው ላይ ሰብስቦ ሞተ፥ ወደ ወገኖቹም ተከማቸ (ስጋዊ እረፍት)  ዮሴፍም በአባቱ ፊት ወደቀ፥ በእርሱም ላይ አለቀሰ፥ ሳመውም። ዮሴፍም ባለመድኃኒቶች አገልጋዮቹ አባቱን በሽቱ ያሹት ዘንድ አዘዘ ባለመድኃኒቶችም እስራኤልን በሽቱ አሹት። አርባ ቀንም ፈጸሙለት የሽቱ መደረጊያው ወራት እንደዚሁ ይፈጸማልና የግብፅም ሰዎች ሰባ ቀን አለቀሱለት።

እንግዲህ ልብ በሉ! ዮሴፍ አባቱን በሽቱ ያሹት ዘንድ እንዳዘዘና ባለመድኃኒቶችም እንዴት አርባ ቀን እንደፈጸሙለት እንዲሁም የግብፅም ሰዎች ሰባ ቀን እንዳለቀሱለት! የእግዚአብሔር አገልጋይ የትም ይሙት-የት ልጆቹ አባታቸው ያዕቆብ በሰራላቸው ትህዛዝና ስርዓት መሰረት የቅዱስ ያዕቆብን አጥንት (በድኑን፤ ሬሳውን) ይዘው ከግብጽ ወደ ከነዓን ምድር አጓዙት በዚያም ባለ ሁለት ክፍል በሆነች ዋሻም ስርዓት ቀብሩን ፈጽመውለታል /ዘፍ ምዕራፍ 49 እና 50/

3. የእስራኤልም ልጆች ከግብፅ ያወጡትና የዮሴፍን አጥንት እውነታ፦ የእስራኤልም ልጆች ከግብፅ ያወጡትን የዮሴፍን አጥንት ያዕቆብ ከሴኬም አባት ከኤሞር ልጆች በመቶ በግ በገዛው እርሻ በሴኬም ቀበሩት እርሻውም ለዮሴፍ ልጆች ርስት ሆነ። ይህም ያዕቆብም ለልጆቹ እንዳዘዛቸው እንደዚያው እንዳደረጉለት ያስረዳናል። /ኢያ 2432-33/

4. ንጉሡ ዳዊት፥ ስለ ሳኦልንና የልጁን ስለ ዮናታን አጥንት ያደረገው እውነታ፦ ዳዊትም ሄደ፥ ሳኦልንም በጊልቦዓ በገደሉ ጊዜ ፍልስጥኤማውያን ከሰቀሉአቸው ስፍራ ከቤትሳን አደባባይ ከሰረቁት ከኢያቢስ ገለዓድ ሰዎች የሳኦልንና የልጁን የዮናታንን አጥንት ወሰደከዚያም የሳኦልንና የልጁን የዮናታንን አጥንት ይዞ መጣ የተሰቀሉትንም ሰዎች አጥንት ሰበሰቡ። የሳኦልንና የልጁን የዮናታንን አጥንት በብንያም አገር በጼላ በአባቱ በቂስ መቃብር ቀበሩት ንጉሡም ያዘዘውን ሁሉ አደረጉ። ከዚያም በኋላ እግዚአብሔር ስለ አገሩ የተለመነውን ሰማ። /2 ሳሙ 2112-14/


5. የኤልሳዕ አጥንት እውነታ፦ ኤልሳዕም ሞተ፥ቀበሩትም። ከሞዓብም አደጋ ጣዮች በየዓመቱ ወደ አገሩ ይገቡ ነበር። ሰዎችም አንድ ሰው ሲቀብሩ አደጋ ጣዮችን አዩ፥ ሬሳውንም በኤልሳዕ መቃብር ጣሉት የኤልሳዕንም አጥንት በነካ ጊዜ ሰውዮው ድኖ በእግሩ ቆመ። /2 ነገ 1320-21/


6. ንጉሡ ኢዮስያስ ስለ እግዚአብሔር ሰው አጥንት የተናገረው እውነታ፦ (ስሙን መጽሐፍ ቅዱስ ስለማይገልጠው ነው። ለማጣቀሻ፥ መጽሐፈ ነገሥት ቀዳማዊ ምዕራፍ 13 ይመልከቱ!)  ኢዮስያስም ዘወር ብሎ በተራራው የነበሩትን መቃብሮች አየ ኢዮርብዓምም በበዓል ጊዜ በመሠዊያ አጠገብ ሲቆም እነዚህን ነገሮች የተነባ የእግዚአብሔር ሰው እንደ ተናገረው እንደ እግዚአብሔር ቃል፥ ልኮ ከመቃብሮቹ አጥንቶቹን አስወጣ፥ በመሠዊያውም ላይ አቃጠላቸው አረከሰውም። ዘወርም ብሎ ወደ ተናገረው ወደ እግዚአብሔር ሰው መቃብር ዓይኖቹን አቅንቶ። የማየው የመታሰቢያ ምልክት ምንድር ነው? አለ። የዚያችም ከተማ ሰዎች። ከይሁዳ ወጥቶ በቤቴል መሠዊያ ላይ ይህን ያደረግኸውን ነገር የተናገረው የእግዚአብሔር ሰው መቃብር ነው ብለው ነገሩት። እርሱም፦ ተዉት፥ ማንም አጥንቱን አያንቀሳቅሰው አለ እነርሱም ከሰማርያ ከወጣው ከነቢዩ አጥንት ጋር አጥንቱን ተዉ። በዚያም የነበሩትን የኮረብታውን መስገጃዎች ካህናት ሁሉ በመሠዊያዎቹ ላይ ገደላቸው፥ የሰዎቹንም አጥንት በመሠዊያዎቹ ላይ አቃጠለ። ወደ ኢየሩሳሌምም ተመለሰ። /2 ነገ 2316-20/


7. በሐዋርያው በቅዱስ ጳውሎሰ አንደበት ስለ ዮሴፍ አጥንት ኑዛዜ እውነታ፦ ኑዛዜ ያለ እንደሆነ የተናዛዡን ሞት ማርዳት የግድ ነውና /ዕብ 916/

8. በሐዋርያው በቅዱስ ጳውሎሰ አንደበት ስለ ዮሴፍ አጥንት ኑዛዜና ትእዛዝ እውነታ፦ ዮሴፍ ወደ ሞት ቀርቦ ሳለ በእምነት ስለ እስራኤል ልጆች መውጣት አስታወሰ፥ ስለ አጥንቱም አዘዛቸው። /ዕብ 1122/

9. ባለ ራእይ ቅዱስ ዮሐንስ ሰለ ቅዱሳን አበው በሚፈልጉበትም ጊዜ ሁሉን በሁሉ ማድረግ በምድር የተሰጣ ሥልጣን ላላቸው ስለ ቅዱ በድን፣ ሬሳ፤ አጥንት እውነታ፦ (ሥልጣን የነበራቸው፣  ሥልጣን ያላቸው፤  ሥልጣን የሚኖራቸው።) ከወገኖችና ከነገዶችም ከቋንቋዎችም ከአሕዛብም የሆኑ ሰዎች ሦስት ቀን ተኵል በድናቸውን ይመለከታሉ፥ በድናቸውም ወደ መቃብር ሊገባ አይፈቅዱም። /ራእ 119/

ስለዚህ ከዚህ ሁሉ ከመጽሐፍ ቅዱስ እውነታ በመነሳት የቅዱሳን አበው አጥንት /አፅም/ ከወገኖችና ከነገዶችም ከቋንቋዎችም ከአሕዛብም የሆኑ ሰዎች ሦስት ቀን ተኵል በድናቸውን ይመለከታሉ፥ በድናቸውም ወደ መቃብር ሊገባ አይፈቅዱም። እንደተባለ፦ የቅዱሳን አበው አጥንት /አፅም/ እየታየ፣ እየተንገረ፤ እየተዳሰሰ ነው። መርሳት የሌለብን ዋና ነጥብ ደግሞ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ በእግዚአብሔር አቆጣጠር ዘንድ፦ እናንተ ግን ወዳጆች ሆይ፥ በጌታ ዘንድ አንድ ቀን እንደ ሺህ ዓመት፥ ሺህ ዓመትም እንደ አንድ ቀን እንደ ሆነ ይህን አንድ ነገር አትርሱ። /2ኛ ጴጥ 3፥8/ ብሎናል።  

የን!

No comments:

Post a Comment